የከተማ መሠረተ ልማት እና ትራንስፖርት ጉዳዮች
የከተማ፣ መሠረተ ልማት እና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ተግባር እና ኃላፊነት
የከተማ፣ መሠረተ ልማት እና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በሚከተሉት ጉዳዮች ላይ ክትትልና ቁጥጥር ያከናውናል፡-
1/ የከተማና ኮንስትራክሽንና መሰረተ ልማትን ተወዳዳሪነትን በቀጣይነት የሚያረጋግጡእና መሰረተ ልማት በውጤታማነትና በቅንጅት መከናወኑን የሚያረጋግጡ፣ የከተማ መሬትን እና ከመሬት ጋር የተያያዘ ሌላ የማይንቀሳቀስ ንብረት ለመመዝገብ የሚያስችሉ ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎችና ህጎችን መዘጋጀታቸውን፣ ለአፈጻጸሙ ከሀገራዊ የልማት አቅጣጫ ጋር የተጣጣመ ዝርዝር መርኃ ግብር መዘጋጀቱን፤
2/ ሀገራዊ የተቀናጀ የመሰረተ ልማት፣ መዋቅራዊ እና ማስተር ፕላን መዘጋጀቱን እና መተግበሩን፤
3/ በሀገር አቀፍ ደረጃ የከተሞች መዋቅራዊና መሰረታዊ ማስተር ኘላን መዘጋጀቱንና አተገባበሩን፤
4/ ለህዝብ ጥቅመም ሲባል የሚለቀቅ የመሬት ይዞታ እና የንብረት ካሳ ቀመር መዘጋጀቱንና ተግባራዊ አፈፃፀም ሂደቱን፤
5/ ከገጠር ወደ ከተማ የሚሸጋገሩ አካባቢዎችን በተመለከተ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎችን፣ የልማት ፕሮግራሞችን መቀረፃቸውን፣ እና ስታንዳርዶችን መውጣታቸውን፤
6/ የተመጣጠነ የከተሞች ዕድገትና የህዝብ አሰፋፈር እንዲኖር ለማድረግ የሚያስችሉ ስልቶች መነደፋቸውን፤
7/ የከተሞችን መሬት በቁጠባ እና በውጤታማነት መጠቀም የሚያስችል ዘመናዊ የአሰራር ስልት መነደፉን እና አተገባበሩን፤
8/ የከተሞችን ፈርጅ እና ሚና መወሰኛ መመዘኛ መውጣቱን፤ የከተሞችን ፅዳት፣ ውበትና አረንጓዴ ልማት ስታንዳርድ መውጣቱንና በስታንዳርዱ መሠረት መተግበሩን፤
9/ ከተሞች የአካባቢያቸው የልማት ማዕከል እንዲሆኑ ሁለገብና የተቀናጀ ድጋፍ መሰጠቱን፣ በጥናት ላይ የተመሰረተ አከታተምና የከተሞች ደረጃ መመዘኛ መውጣቱን እንዲሁም የከተሞች አገልግሎት አሰጣጥ እንዲሻሻል የአቅም ግንባታ እገዛ መደረጉን፤
10/ የነፃ ገበያ ስርዓት ለማረጋገጥ የሚያስችል፣ ግልፅነትና ተጠያቂነት የሚያሰፍን የካዳስተር እና የማይንቀሳቀስ ንብረት ግብይት ስርዓት እንዲገነባ መደረጉን እንዲሁም በከተሞች ፍላጎትን መሰረት ያደረገ የለማ መሬት አቅርቦት ለማረጋገጥ ተገቢው ድጋፍ እየተሰጠ ስለመሆኑ፤
11/ የከተሞች ልማት ፋይናንስ ማጠናከሪያ ስርዓት ተግባራዊ ተደርጎ ዘላቂ ልማትን እያረጋገጠ መሆኑን፤
12/ የከተሞች ልማት ከገጠር ልማት ጋር ተቀናጅቶ የሚከናወንበት መንገድ መጠናቱንና ከክልሎች ጋር በመተባበር ተግባራዊ መደረጉን፤
13/ የዜጎች የመኖሪያ ቤት አቅርቦትን ለማሟላት የሚያስችል ስርዓት መዘርጋቱን፣
14/ የተመጣጠነ የከተሞች እድገትና የህዝብ አስፋፈር እንዲኖር የሚያስችል ስልት በፌደራልና በክልል መንግስታት ቅንጅት ተግባራዊነቱ ተረጋግጦ ዘላቂ ልማትን እያስገኘ መሆኑን፤
15/ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ በብቃት እንዲገነባ ምቹ ሁኔታ መፈጠሩን፤
16/ ለኮንስትራክሽን ስራዎች ደረጃ መውጣቱ እና በአግባቡ እየተከበረ መሆኑን፤
17/ በአገር ውስጥ የሚመረቱ የኮንስትራክሽን ዕቃዎች አይነትና ጥራት ለማሻሻል የሚደረገውን እንቅስቃሴ፤
18/ አገር በቀል የኮንስትራክሽን ድርጅቶች ብቃት፣ ቀጣይነት እና የገበያ ተወዳዳሪነትን ለማረጋገጥ የሚደረገው ጥረት ስኬታማ መሆኑን፣
19/ በኮንስትራክሽን ዘርፍ ለሚሰማሩ የምዝገባ፣ ፈቃድ፣ የሙያ ብቃት እና የምስክር ወረቀት ስርዓቱ ብቃትን እና ተወዳዳሪነትን በሚያረጋግጥ አግባብ እየተመራ መሆኑን፤
20/ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ዘርፍ ልማትንና ተወዳዳሪነትን በቀጣይነት የሚያረጋግጡ ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎችና ህጎችን መውጣታቸውን፣ አፈጻጸሙ ከሀገራዊ የልማት አቅጣጫ ጋር የተጣጣመ ዝርዝር መርኃ ግብር መዘጋጀቱን አና ተግባራዊነቱን፤
21/ የሀገሪቱን የልማት ስትራቴጂዎች ተግባራዊ ለማድረግ፣ የልማት ማዕከላትንና የዕድገት ኮሪደሮችን የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ፍላጐት ለማሟላት የየብስ፣ የአየርና የባህር ትራንስፖርት አገልግሎቶች የተቀናጁ፣ ቀልጣፋና ተደራሽ መሆናቸውን፤
22/ የትራንስፖርት አገልግሎቶች የአገሪቱን የልማት ስትራቴጂ በተሟላ ሁኔታ ለማገልገል በሚያስችል መልኩ በተቀናጀ መንገድ መስፋፋታቸውንና ከሌሎች ዘርፎች ጋር ተደጋግፈው የሚያድጉበት አሠራር መዘርጋቱን እና ውጤታማነቱን፤
23/ የትራንስፖርት መሰረተ ልማቶች ስታንዳርድ የወጣላቸው መሆኑን እንዲሁም የአጠቃቀም፣ የአያያዝና የአስተዳደር ስርዓቶች መወሰናቸውን እና ተግባራዊ መሆናቸውን፤
24/ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክ አገልግሎቶች አስተማማኝና ደህንነታቸው የተጠበቀ መሆናቸውን ለማረጋገጥ የሚያስችል የቁጥጥር ስልት መዘርጋቱን እና ተግባራዊ መሆኑን፤
25/ የትራንስፖርት መሠረተ ልማቶች መዘርጋታቸውን፣ መስፋፋታቸውንና መጠገናቸውን እንዲሁም በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ ጥራታቸውን ጠብቀው በውጤታማነት መከናወናቸውን፤
26/ የሚከታተላቸውና የሚቆጣጠራቸው ተቋማትን የሚመለከቱ ፖሊሲዎች፣ ህጎች፣ ስትራቴጂዎች እና እቅዶች በአግባቡ በሥራ ላይ መዋላቸውን፤
27/ የሚከታተላቸውና የሚቆጣጠራቸው ተቋማት የተመደበላቸውን በጀት በአግባቡና በውጤታማነት በስራ ላይ ማዋላቸውን፡፡