የውጭ ግንኙነት እና ሰላም ጉዳዮች
የውጭ ግንኙነት እና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ተግባር እና ኃላፊነት
የውጭ ግንኙነት እና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በሚከተሉት ጉዳዮች ላይ ክትትልና ቁጥጥር ያከናውናል፡-
1/ የአገርና የሕዝብ ሰላም፣ ድህነትና ነፃነት እንዲከበሩ የሚያስችል ስልት የተነደፈ መሆኑና አስፈላጊው ግንዛቤና የንቅናቄ ስራ መከናወኑን፤
2/ በየትኛውም የአገሪቱ ክፍሎች የሚኖሩ ዜጎች መብትና ነፃነታቸው በተሟላ እንዲከበርና ጥበቃ እንዲያገኝ የፌደራሉ መንግስት ከክልል መንግስት ጋር በመተባበር እየሰራ መሆኑን፤
3/ በወሳኝ አገራዊ ጉዳዮች ብሔራዊ መግባባት ለመገንባት የሚያስችሉ ተግባራት እየተከናወኑ መሆኑን፤
4/ መንግስት የሚፈራረማቸው ዓለም አቀፍ ስምምነቶች የአገሪቱን ብሔራዊ ጥቅም የሚያረጋግጡና ሉዓላዊነትን የሚያስከብሩ፣ ከውጭ ግንኙነት መርሆና ፖሊሲ ጋር የተጣጣሙ መሆኑን፤
5/ መንግስት የሚያካሂዳቸው የውጭ ግንኙነት ተግባራት የአገሪቱን ዘላቂ ሰላም፣ ዲሞክራሲና ልማት የሚያረጋግጡ መሆኑን፤
6/ የውጭ ጉዳይ ፖሊሲና ስትራቴጂ እንዲሁም እቅዶችና ህጎች በአግባቡ በስራ ላይ መዋላቸውንና የሚፈለገውን ውጤት ማስገኘታቸውን፤
7/ የአገሪቷ የግዛት ሉዓላዊነት እየተከበረ መሆኑን፤
8/ የአገሪቱን ሉዓላዊነት ሊያስከብር የሚችል የብሔር፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦችን ተዋፆ የጠበቀ የመከላከያ ሰራዊት መደራጀቱን፤
9/ የአገር መከላከያ ሰራዊት አባላት የስራ ሁኔታና አስተዳደር በአግባቡ መጠበቁን፤
10/ ከሌሎች አገራት ጋር የሚደረጉ ወታደራዊ ስምምነቶችና አፈፃፀሞች፤
11/ ክፍለ አህጉራዊ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፍ የሰላም ስምምነቶችን፣ ግዴታዎችና አፈጻጸሞችን በተመለከተ፤
12/ የአገር መከላከያ ሰራዊት በሌሎች አገራት የሚያካሂዳቸውን የሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች፤
13/ ለሕገ-መንግሥቱና ለሕገመንግሥታዊ ስርዓቱ በታማኝነትና በፅናት የሚቆም፣ አገራዊና ዓለም አቀፋዊ ተጨባጭ ሁኔታዎችን በማገናዘብ ዘመናዊና ጠንካራ ብሔራዊ የመረጃና ደህንነት አገልግሎት መገንባቱን፤
14/ ጥራት ያለው መረጃ በማቅረብና አስተማማኝ የደህንነት አገልግሎት በመስጠት የአገሪቷ ብሔራዊ ደህንነት እየተጠበቀ መሆኑን፤
15/ በግለሰቦችና በቡድኖች መካከል የሰላም፣ የመከባበርና የመቻቻል ባህል እንዲዳብር ለማድረግ የሚከናወኑ ተግባራትን፣
16/ የህዝብ ሠላም መጠበቁን እንደዚሁም አለመግባባቶችንና ግጭቶችን ለመከላከልና በዘላቂነት ለመፍታት የሚያስችል አሠራርና እንቅስቃሴ መኖሩን፤
17/ በፌደራል መንግስትና በክልሎች መካከል በመግባባትና በአጋርነት ላይ የተመሠረተ መልካም ግንኙነትና ትብብር እንዲጠናከር የሚደረገውን እንቅስቃሴ፤
18/ የአገሪቱን የመከላከያ እና የብሔራዊ መረጃና ደህንነት ፓሊሲዎችና ስትራቴጂዎች አፈፃፀምን፤
19/ የሚከታተላቸውና የሚቆጣጠራቸው ተቋማትን የሚመለከቱ ፖሊሲዎች፣ ህጎች፣ ስትራቴጂዎች እና ዕቅዶች በአግባቡ በሥራ ላይ መዋላቸውን፤
20/ የሚከታተላቸውና የሚቆጣጠራቸው ተቋማት የተመደበላቸውን በጀት በአግባቡና በውጤታማነት በስራ ላይ ማዋላቸውን፡፡
የውጭ ግንኙነት እና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሌሎች ተግባራት
1/ ቋሚ ኮሚቴው ለምክር ቤቱ የሚቀርቡ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች ከህገ-መንግስቱ እና ከአገሪቷ የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ ጋር የተጣጣሙ መሆናቸውን ይመረምራል፡፡
2/ ቋሚ ኮሚቴው ምክር ቤቱ ከሌሎች አገሮች ምክር ቤቶች እና ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር የሚያካሂዳቸውን የሁለትዮሽ እና የባለብዙ ወገን የፓርላማ ዲፕሎማሲ ግንኙነቶችን ያስተባብራል፣ አፈፃፀሙንም ይከታተላል፡፡