ምክር ቤቱ የስታርትአፕ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ ለሚመለከተው ቋሚ ኮሚቴ መራ

 (ዜና ፓርላማ) ሰኔ 10 ቀን፣ 2017 .ም፤ ምክር ቤቱ ባካሄደው ጉባኤ የስታርትአፕ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ ለሚመለከተው ቋሚ ኮሚቴ መርቷል።

ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ የመንግሰት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር የተከበሩ ተስፋዬ በልጅጌ (/) ለምክር ቤቱ ማብራሪያ አቅርበዋል፡፡

በማብራሪያቸውም ረቂቅ አዋጁ ኢኖቬሽን ነባር አሠራሮችን፣ የምርትና የአገልግሎት ሂደቶችንና ምርቶችን በሳይንሳዊ መንገድ በመቀየር ሰዎች ሕይወታቸውን በተሻለ መንገድ እንዲመሩ የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ሀገራት ይህን ከባቢያዊ ሥርዓት ለመፍጠር የሚያስችሉ ሕጎች ማውጣታቸውን እና በዚህ ዘርፍ ከተሰማሩ ከሃሳብ አፍላቂዎች ጀምሮ መዋዕለ ንዋያቸውን ኢንቨስት ላደረጉና ለሚያደርጉ ግለሰቦችና ድርጅቶች የአገራቱ አቅም የሚፈቅደውን እና ተገቢ ነው ያሉትን የማበረታቻ ማዕቀፍ አዘጋጅተው ወደ ሥራ ማስገባታቸውንም አብራርተዋል፡፡

በአገራችን ኢትዮጵያ ይህን ሥርዓት መፍጠር ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂን ከማስረጽና በኢኮኖሚው ውስጥ ሊያመጣ የሚችለውን አዎንታዊ ውጤት የሚመጣ፣ በተለይም ለወጣቶች የሥራ ዕድል የመፍጠር አቅሙም ከፍተኛ የሆነ እንዲሁም በአገር የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ሊያመጣ የሚችለውን ለውጥ ታሳቢ በማድረግ የሕግ ማዕቀፍ ለመፍጠር አስፈላጊ መሆኑንም ነው የተከበሩ ተስፋዬ በልጅጌ (/) የገለጹት።

የምክር ቤት አባላት በበኩላቸው ረቂቅ አዋጁ ሀሳብን ወደ ገንዘብ የሚቀየርበትን መንገድ የሚፈጥር እና ፈጠራን የሚያበረታታ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ምክር ቤቱ በረቂቅ አዋጁ ላይ በስፋት ከተወያየበት በኋላ ረቂቅ አዋጅ ቁጥር 2320/2017 ሆኖ ለዝርዝር ዕይታ ለሰው ሃብት ልማት፣ ስራ ስምሪት እና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በሙሉ ድምጽ መርቷል፡፡