ምክር ቤቱ የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ረቂቅ አዋጅን መርምሮ ለሚመለከተው ቋሚ ኮሚቴ መራ
(ዜና ፓርላማ) መጋቢት 9/2017 ዓ.ም፣ የኢፌዴሪ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው 20ኛ መደበኛ ስብሰባ የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ረቂቅ አዋጅን መርምሮ ለሚመለከተው ቋሚ ኮሚቴ መርቷል።
በምክር ቤቱ የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር የተከበሩ ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ አጭር ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር የቅድመ አደጋ፣ የአደጋ ወቅትና ድህረ አደጋ ተግባራትን ውጤታማ ለማድረግ የፌደራልና የክልል አስተዳደር ተቋማት የውስጥ አቅም ለመገንባት፤ ቅጽበታዊ አደጋ ሲከሰትና ከአቅም በላይ ሲሆንም የአስቸኳይ ጊዜ እወጃ ስርአት ለመዘርጋትና ተግባራዊ ለማድረግ እንዲሁም የሰብአዊ ድጋፍ፣ የዘላቂ ልማት እና የሰላም ግንባታ እቅዶችን ለማስተሳሰር የሚያስችል የተሟላ የህግ ማዕቀፍ ለመዘርጋት እንዲያስችል የተዘጋጀ ረቂቅ አዋጅ መሆኑን ገልጸዋል።
ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ምክር ቤት መቋቋምን የተመለከቱ ድንጋጌዎች እና ስለ ኮሚሽኑ ተግባርና ኃላፊነት የምክር ቤቱ ስልጣንና ተግባራት፣ ስለፌደራል መሪ ዘርፍ ተቋማት እና የክልል መንግስታት ተግባርና ኃላፊነት፣ ስለአደጋ ተጋላጮችና ተጎጂዎች መብትና ግዴታ እንዲሁም ስለ ኢትዮጵያ አደጋ ስጋት ምላሽ ፈንድ መቋቋም የሚመለከቱና ሌሎች ድንጋጌዎች መካተታቸውን የተከበሩ ተስፋዬ (ዶ/ር) ገልጸዋል።
የምክርቤት አባላትም አዋጁ የሚደረጉ ድጋፎች በተቀናጀ መልኩ እዲደረጉና ለተጎድጂዎች እኩል ተደራሽ ለማድረግ እንዲሁም ከእርዳታ ጠባቂነት በመላቀቅ እራስን ለመቻል አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል ።
ረቂቅ አዋጁ የኢትዮጵያ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ረቂቅ አዋጅ ቁጥር 16/2017 ሆኖ በሙሉ ድምጽ ለውጭ ግንኙነትና ለሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለዝርዝር እይታ ተመርቷል።
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives