ምክር ቤቱ በፌዴራል መንግስት የ2018 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት ላይ ተወያየ
ምክር ቤቱ በፌዴራል መንግስት የ2018 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት ላይ ተወያየ
(ዜና ፓርላማ) ሰኔ 03፣ 2017 ዓ.ም.፤ ምክር ቤቱ በፌዴራል መንግስት የ2018 በጀት ዓመት ረቂቅ በጀት ላይ ተወያይቷል፡፡
ረቂቅ በጀቱን በተመለከተ የበጀት መግለጫውን የገንዘብ ሚኒሰትሩ ክቡር አቶ አህመድ ሽዴ ለምክር ቤት አባላት አቅርበዋል፡፡
ረቂቅ በጀቱ ለምክር ቤቱ 1 ነጥብ 93 ትሪሊዮን ብር ሆኖ የቀረበ ሲሆን፣ 1 ነጥብ 2 ትሪሊዮን ብር ለመደበኛ ወጪ፣ 4 መቶ 15 ቢሊዮን ብር ለካፒታል ወጪ፣ 3 መቶ 15 ቢሊዮን ብር ለክልል መንግስታት ድጋፍ እንዲሁም 14 ቢሊዮን ብር ደግሞ ለክልሎች የዘላቂ ልማት ግቦች ማስፈፀሚያ ድጋፍ እንደሚውል ሚኒስትሩ ጠቅሰዋል፡፡
የ2018 በጀት የተጀመሩ የልማት ስራዎችን ለማስቀጠል፣ ማሕበራዊ ወጪዎችን ለመሸፈን፣ የዕዳ ስረዛን ወደ መካከለኛ ደረጃ ለማውረድ እና ማክሮ ኢኮኖሚውን ማረጋጋት ላይ ያተኮረ እንደሚሆን ነው ያብራሩት፡፡
እንዲሁም፣ የመንግስትን የገቢ አሰባሰብ ለማሳደግ፣ የክልል መንግስታት ገቢን ለማሳደግ እና የታክስ አስተዳደርን ለማጠናከር በልዩ ትኩረት እንደሚሰራ ክቡር አቶ አህመድ አብራርተዋል፡፡
ረቂቅ በጀቱ የ10 ዓመቱን መሪ የልማት እቅድን እና የተሟላ ማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያን ታሳቢ ባደረገ መልኩ እንደተዘጋጀ ጨምረው አብራርተዋል፡፡
በካፒታል በጀቱ መንገዶችን እና ትምህርትን ለማስፋፋት፣ መስኖና የግብርና ስራዎችን ለማዘመን፣ የገጠር እና ከተማ ምግብ ዋስትና እና ልማታዊ ሴፍቲኔትን ለማረጋገጥ እንደሚውል ሚኒስትሩ አብራርተዋል፡፡
እንዲሁም፣ በጀቱ የጤናውን ዘርፍ ለማስፋት፣ በጦርነቱ ጉዳት የደረሰባቸውን አካባቢዎች መልሶ ለመቋቋም ፣ ለመንግስት ቢሮ ግንባታ እና ለንጹህ መጠጥ ውሃ እንደሚውል ነው አቶ አህመድ ያስረዱት፡፡
በ2018 በጀት ዓመት የ8 ነጥብ 9 በመቶ የኢኮኖሚ እድገት እንደሚመዘገብ መተንበይ መቻሉን ሚኒስትሩ ገልፀዋል።
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives