አዋጁ ሽብርተኝነትንና ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚያስችል እና ከዓለም አቀፍ ህጎች ጋር የተጠጣመ መሆኑ ተገለጸ
አዋጁ ሽብርተኝነትንና ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚያስችል እና ከዓለም አቀፍ ህጎች ጋር የተጠጣመ መሆኑ ተገለጸ
(ዜና ፓርላማ) ሰኔ 10 ቀን፣ 2017 ዓ.ም፤ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት ዛሬ ባካሄደው 37ኛ መደበኛ ስብሰባው በወንጀል የተገኘ ንብረት ሕጋዊ ማስመሰል እና ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳት ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የቀረበውን ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ መርምሮ አፅድቋል፡፡
የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ ኢሳ ቦሩ የማሻሻያ ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ በኮሚቴው የተዘጋጀውን ሪፖርትና የውሳኔ ሀሳብ ለምክር ቤቱ አቅርበዋል፡፡
የተከበሩ አቶ ኢሳ ባቀረቡት የውሳኔ ሀሳብ ይህ የማሻሻያ አዋጅ በወንጀል ተግባር የተገኘ ገንዘብን ወይም ንብረትን ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብ እና ሽብርተኝነትን በገንዘብ የመርዳት ወንጀል ድርጊትን ለመከላከልና ለመቆጣጠር በሚደረገው ዓለም አቀፍ ጥረት ላይ ሀገራችን ያላትን ድርሻ በአግባቡ እንድትወጣ ሊያደርጋት የሚችል ነው ብለዋል፡፡
አዋጁ አመንጭ ወንጀሎችን በግልፅ ያስቀመጠና ለአፈፃፀም አስቸጋሪና ለትርጉም ተጋላጭ የነበሩትን ጉዳዮች ያስተካከለ፣ የወንጀል ድርጊቱን ክብደት እና ቅለት ባልተመዘነበት ሁኔታ ይጣል የነበረውን ቅጣት መልክ ሊያስይዝ በሚችል አግባብ የተዘጋጀ መሆኑንም ነው ያብራሩት፡፡
የምክር ቤት አባላት በበኩላቸው የረቂቅ አዋጁ በርካታ አንቀጾች የተሻሻሉ በመሆኑ ማሻሻያ አዋጁ ከሚባል የቀድሞ አዋጅ 780/2005 ተሸሮ በአዲስ የተተካ ቢባል፣ ረቂቅ አዋጁ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ጋዜጠኞችና ነጋዴዎችን የሚጎዳ እንዳይሆን ሲሉ ስታቸውን ገልፀዋል፡፡
የተከበሩ አቶ ኢሳ ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ የሰጡ ሲሆን፤ በሥራ ላይ የነበረው አዋጅ ቁጥር 780/2005 በጠቅላላው 58 አንቀጾች የነበሩ ሲሆን በረቂቅ አዋጁ ላይ መሰረታዊ ለውጥ እና ማሻሻያ የተደረገባቸው አንቀፆች 14 ብቻ በመሆናቸው አዋጁን ሙሉ በሙሉ ከመቀየር ይልቅ ማሻሻያ ማድረጉ ተገቢ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
አክለውም አዋጁ ወንጀልን እና ሽብርተኝነትን በገንዘብ የሚደግፉ ማንኛውንም ዜጋና ቡድኖችን ተጠያቂ የሚያደርግ እንጂ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ጋዜጠኞችና ነጋዴዎችን ብቻ በመየት ተጠያቂ እንደማያደርግም ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
በመጨረሻም ምክር ቤቱ በረቂቅ አዋጁ ላይ በስፋት ከተወያየበት በኋላ በወንጀል የተገኘ ንብረት ሕጋዊ ማስመሰል እና ሽብርተኝነትን በገንዘብ መርዳት ወንጀልን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የቀረበውን ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ፤ አዋጅ ቁጥር 1387/2017 አድርጎ በሶስት ተቃውሞ እና በአንድ ድምፀ ተአቅቦ በአብላጫ ድምፅ አፅድቋል፡፡
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives