ኢንዱስትሪው የአርሶ-አደሩን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ በሚያስችል መልኩ ችግሩን መፍታት እንዳለበት ኮሚቴው ጠቆመ

(ዜና ፓርላማ)፣ ሚያዚያ 01፣ 2013 ዓ.ም.፤ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የገቢ፣ በጀት እና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የአዳማ የግብርና መሳሪያዎች ማምረቻ ኢንዱስትሪ አርሶ-አደሩን በቴክኖሎጅ ተጠቃሚ ለማርግ እንዲችል ያገጠሙትን ችግሮች በፍጥነት መፍታት አለበት በማለት ጠቁሟል፡፡

ቋሚ ኮሚቴው ይህንን የገለጸው የአዳማ የግብርና መሳሪያዎች ማምረቻ ኢንዱስትሪ የስራ እንቅስቃሴን አስመልክቶ በቦታው የመስክ ምልከታ ባደረገበት ወቅት ነው ፡፡

በምልከታውም የተሰብሳቢ ሂሳቦች ወቅታቸውን ጠብቀው አለመሰብሰባቸው እና የእርሻ መሳሪያዎች ሃብት ክምችት ወደ ግብርናው ክፍለ-ኢኮኖሚ አለመድረሱ አርሶ-አደሩ በቴክኖሎጅ ታግዞ ስራውን መስራት እንዳልቻለ የቡድኑ አስተባባሪ አቶ አያሌው አይዛ  ተናግረዋል፡፡

ማምረቻ ኢንዱስትሪው ለሰባት አመታት በዱቤ ሸጦ ያልሰበሰበው ገንዘብ ከ1 ነጥብ 9 ቢሊዮን ብር በላይ መድረሱ እንዲሁም የእርሻ መሳሪያ ክምችቱ በገንዘብ ሲገመት ከ3 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር በላይ ይዘው መቀመጣቸው በውይይቱ ተገልጿል፡፡

የግብርና መሳሪያዎች ማምረቻ ኢንዱስትሪው ባጋጠሙት ችግሮች ቴክኖሎጂን ወደ አርሶ አደሩ ማድረስ ላይ አፈጻጸሙ ዝቅተኛ መሆኑን አስተባባሪው ጠቅሰው፣ ከውጭ ወደ ሃገር ከገቡ የቆዩና በቂ መለዋወጫ የሌላቸው የሚወገዱ ትራክተሮች ስለመኖራቸውም አቶ አያሌው አክለው ገልጸዋል፡፡

የማምረቻ ኢንዱስትሪው ያጋጠሙትን ችግሮች በፍጥነት ፈትቶ አርሶ-አደሩ የቴክኖሎጅ ተጠቃሚ እንዲሆን አስገንዝበው፣ ቋሚ ኮሚቴውም አስፈላጊውን እገዛ እንደሚያደርግላቸው አስተባባሪው ጠቅሰዋል ፡፡

የኢንዱስትሪው ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ድሪባ ሁንዴ በበኩላቸው የእርሻ መሣሪያዎቹ ሲገዙ ተጨባጭ የሀገሪቷን መልክዓ-ምድር ነባራዊ ሁኔታ ጥናት ሳይደረግ ግዥ መከናወኑ ቴክኖሎጅዎቹ ወደ አርሶ- አደሩ አለመሰራጨታቸውን ገልጸዋል፡፡

የተገዙት የትራክተር ተቀጽላዎች/ መለዋወጫዎች/ የጥራት ችግር ያለባቸውና ከትራክተሮች ቁጥር ጋር በአሃዝ ተመጣጣኝ አለመሆናቸውንም አቶ ድሪባ ተናግረው፣ ችግሮቹን ከሚመለከተው አካል ጋር በመወያየት ፈትተው የአርሶ-አደሩን የቴክኖሎጅ ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ እንደሚሰሩ አብራርተዋል፡፡

በፋንታዬ ጌታቸው