(ዜና ፓርላማ)፣ ነሐሴ 9፣ 2015 ዓ.ም.፤ አዲስ አበባ፤ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ሀገራዊ አጀንዳዎችን እና የምክክሩን ተሳታፊዎች የመለየት ሥራ አጠናክሮ መቀጠሉ ተገለጸ፡፡ 

ኮሚሽኑ እየሰራቸው ያሉትን በርካታ ሥራዎች በተሠጠው ሀገራዊ ተልዕኮ መሠረት በማድረግ ሥራዎቹን ለሕዝብ በሚዲያ ተደራሽ ለማድረግ አደረጃጀቱን ሊያጠናክር  እንደሚገባ ምክትል አፈ-ጉባኤ የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ በዶ ገልጸዋል፡፡ 

የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑን አጀንዳዎችና የምክክሩን ተሳታፊዎች የመለየት ሥራ አጠናክሮ መቀጠሉን የተገለጸው ኮሚሽኑ በ2015 በጀት ዓመት ያከናወናቸውን ሥራዎች በተመለከተ የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት ለምክር ቤቱ ባቀረበበት ወቅት ነው፡፡

ኮሚሽኑ እስከአሁን በአምስት ክልሎች የሀገራዊ አጀንዳዎች እና የምክክሩን ተሳታፊዎች የመለየት ሥራ የሰራ ሲሆን የመጀመሪያ ዙር ሥራውን በማጠናቀቅ ከመጀመሪያ ዙር ያገኛቸውን ልምዶች መነሻ በማድረግ በሌሎች ክልሎች በቀጣይ ዙር የአጀንዳና የምክክሩ ተሳታፊዎች የመለየት ሥራ እንደሚሰራ አስታወቋል፡፡ 

በመሆኑም ቀጥሎ ሁሉን ባሳተፈ ሁኔታ በውይይትና ምክክር ወደ ተግባር ምዕራፍ ለመግባት ዝግጅት እያደረገ መሆኑን ታወቋል፡፡ እስከአሁን በሀገር ደረጃ የሚያወዛግቡንን ጉዳዮች በመለየትና በመወያየት እንደ ሀገር ከግጭትና ቀውስ አዙሪት ውስጥ ለመውጣት እንዲቻል በኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት የተጣለበትን ታላቅ ኃላፊነት ለመወጣት ቁርጠኛ መሆኑም ኮሚሽኑ ገልጿል፡፡

የመንግስት ተጠሪ ሚንስትር የተከበሩ አቶ ተስፋዬ በልጅጌ በበኩላቸው ኮሚሸኑ በበጀት ዓመቱ ያከናዎናቸውን ስራዎች አድንቀው፤ ተቋማዊ አሠራሮችን ማዕከል በማድረግ እና ሁሉንም የሚዲያ አማራጮች በመጠቀም የምክክር ኮሚሽኑ ሁሉን የሚያሳትፍ መሆን ይገባል ብለዋል፡፡ 

ኮሚሽኑ ሕዝብ የጣለበትን ተልዕኮ በሚገባ ግቡን እንዲመታ ለማስቻል በሚዲያ ባለሙያዎች የታገዘ መሆን እንዳለበት የተከበሩ አቶ ተስፋዬ አስረድተዋል፡፡ ኮሚሽኑ ተቋማዊ በሆነ መንገድ  ሚዲያን ተጠቅሞ የኮሚሽኑን አዋጅ፣ ስትራቴጅዎች ፣ አፈጻጸሞች እና መልዕክቶች ለሕዝቡ ለማስተዋወቅ  አቅዶ መንቀሳቀስ እንዳለበት አስገንዝበው፤ ለተግባራዊነቱም መንግስት እገዛ ያደርጋል ብለዋል፡፡

የመንግሥት ተጠሪ ሚንስተሩ የተከበሩ አቶ ተስፋዬ በልጅጌ እንደገለጹት በቀረበው ዓመታዊ ሪፖርት አጅግ አበረታች ሥራዎች የተሰሩ እንደሆነ መረዳታቸውን በሚዲያና የኮሚዩኒኬሽን ሥራዎች የመወያያ አጀንዳዎችን በመለየት ከተለያዩ የሕብረተስብ ክፍሎች ጋር በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ለማወያየት መቻሉ አበረታች ስራዎችን እየሠራ መሆኑን መረዳታቸውን ገለጸዋል፡፡ በቀጣይም የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ሥራዎች በፍጥነት መሥራት እንደሚገባና በተያዘው የግዜ ሰሌዳ መሠረት እንዲተገበር አመላክተዋል፡፡ በዚህም እጅግ መሠረታዊና ሀገራዊ አጀንዳ ላይ ትኩረት ማድረግ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡

ኮሚሽኑ የትኩረት መስኮችን በመለየት የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ሥራውን በተገቢው ሁኔታ ለመፈጸም የሚያስችሉትን ሥራዎች እየሠራ መሆኑን የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽኑን ዓመታዊ የሥራ ክንዉኑን ያቀረቡት ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ አሳታውቀዋል፡፡ 

የትኩረት መስኮች ተብለው የተጠቀሱት የላቀ ሀገራዊ ምክክር፣ ስትራቴጂዊ አጋርነት ትስስር፣ የላቀ የሕዝብ ተሳትፎ ማድረግ እንዲቻል የሦስት ዓመታት ስትራቴጂክ ዕቀድ አዘጋጅቶ ወደ ትግበራ መገባቱ፤ ኮሚሽኑ መዋቅራዊ አደረጃጀት አዘጋጅቶ የሰው ኃይል ለሟሟላት ጥረት ማድረጉ በጥንካራ ጎን የሚወሰዱ ጉዳዮች ሲሆኑ ኮሚሽኑ ከነበሩ የጸጥታ ጉዳዮች ጋር በተገናኘ  በተፈለገው ፍጥነት ለማከናወን የሚያስቸግሩ ጉዳዮች ቢኖሩም ሀገራዊው የምክክር መድረክን በቀጣይ ለማሰካትና በሀገር አቀፍ ደረጃ በሰፊው ለመስራት የሚያስቸሉ እጅግ በርካታ ሥራዎች ተሰርተዋል፡፡

ከነዚህም ውስጥ ተባባሪ አካላትን እና መድረኮች የሚካሔዱባቸውን ቦታዎች የመለየት፣ ለሥልጠና የሚያስፈልጉ ግብዓቶችን እንዲሟሉ የማድረግ እንዲሁም ስለምክክር ኮሚሽኑ የአሠራር ሒደት በሕብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤ መፍጠር እንዲቻል በርካታ ሥራዎች በአበረታች ሁኔታ እየተሰሩ መሆናቸውን ነገር ግን ከሚዲያና የኮሚዩኒኬሽን ስራዎች አንጻር ድጋፍ የሚያስፈልግ መሆኑንና የሕዝብና የመንግሥት ዋነኛ የትኩረት አጀንዳ እንዲሆን ማድረግ እንደሚያስፈልግ አሳስበዋል፡፡ 

በተጨማሪም የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑን ተግባራት ሀገራዊ ፣ ክልላዊና የማሕበረሰብ ሚዲያዎች የሕዝብ ዋነኛ አጅንዳ አድረግው መሥራት እንደሚገባቸው ገልጸዋል፡፡

ኮሚሽኑ የስትራቴጂካዊ አጋሮችን የማሰደግ ትስስር ለመስራት ከበጎ አድርጎት ድርጅቶች፣ ከፖለቲካዊ ድርጅቶች መማክርት፣ የመምህራን ማህበር፣ የኢትዮጲያ የሐይማኖት ተቋማት ጉባኤ፣ የኢትዮጲያ ዕድሮች ማሕበርና ሌሎች የሕዝብ ማሳተፊያ የትስስር መንገዶችን በመጠቀም ሁሉንም ተዋንያን ባለድርሻ  አካላት አካታች በሆነ መልኩ የምክክር ኮሚሽኑን ሥራ ለማሳከት ሰፊ ሥራ እንደሚሰራም ተመላክቷል፡፡

እስከአሁን በኮሚሽኑ የሕዝባዊ ውይይት በተደረገባቸው ክልሎች ውስጥ በተለያዩ ወረዳዎች የተሳተፉ 51 435 ዜጎች መሆናቸውን የገለጹት ዋና ኮሚሽኑ ውይይት በተደረገባቸው ቦታዎች ሕዝቡ በኮሚሽኑ ላይ ትልቅ ተስፋ የጣለ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡ 

የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን ኣርዓያ በበኩላቸው፤ የኮሚሽኑን ስራዎች ተደራሽ ለማድረግ ከተለያዩ ማኅበራዊ እና የግል ሚዲያ ተቋማት እንዲሁም ከክልሎች ሚዲያ ተቋማት ጋር በመነጋገር ዘገባዎች እንዲሰሩ ማደረጉን  አስረድተዋል፡፡

ይሁን እንጂ የኮሚሽኑን ስራዎች ለሕዝቡ ለማስተዋወቅ እና ምክክሩን ለሁሉም ተደራሽ  ለማድረግ የሚዲያ ተደራሽነት ችግር እንቅፋት እንደሆነባቸው አብራርተው፤ ችግሩን ለመፍታት ምክር ቤቱ እገዛ እንዲያደርግላቸው ጠይቀዋል፡፡ 

ኮሚሽኑ ስራውን ለማሳለጥ ከትግራይ ክልል በስተቀር የትውውቅ፣ ተሳታፊዎችን የመለያና የአጀንዳ አሠባሠብ ዘዴ መድረኮች መካሄዳቸውን ፕሮፌሰሩ አብራርተዋል፡፡

የፀጥታ መደፍረስ እና የሎጅስቲክስ መጓተት ኮሚሽኑ ዕቅዱን ተከትሎ ስራዎቹን እንዳያሳካ ማድረጋቸውን ኮሚሽነሩ ጠቅሰዋል፡፡

በመጨረሻም ኮሚሽኑ አካታች፣ አሳታፊ እና ገለልተኛ ሆኖ ምክክሩን በፍጥነት በመጀመር ሀገራዊ ግቡን እንዲመታ የኮሚሽኑ አመራሮች ከመቼውም ጊዜ በላይ በርትተው እንዲሰሩ የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ አሳስበው፤ የኮሚሽኑ ስራዎች በሚዲያ ተደራሽ ሆነው ምክክሩ ሁሉንም የሕብረተሰብ ክፍል ያማከለ እንዲሆን ምክር ቤቱ እገዛ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።

ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡- 
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament 
በዩቲዩብ https://www.youtube.com/@FDREHOPR 
በቴሌግራም https://t.me/ParlamaNews 
በትዊተር http://twitter.com/fdrehopr 
በዌብሳይት www.hopr.gov.et ይከታተሉ