ኮሚሽኑ የሰራተኞቹን ቅሬታ መፍታት የሚያስችል በጥናት የተደገፈ አሰራር ሊኖረው እንደሚገባ ቋሚ ኮሚቴው አሳሰበ
ኮሚሽኑ የሰራተኞቹን ቅሬታ መፍታት የሚያስችል በጥናት የተደገፈ አሰራር ሊኖረው እንደሚገባ ቋሚ ኮሚቴው አሳሰበ
ዜና ፓርላማ ሚያዚያ 5 ቀን 2013 ዓ.ም፤ በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኦሮሚያ እና በሲዳማ አካባቢ የብሔራዊ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽንን የስራ እንቅስቃሴ ተዘዋውሮ ተመልክቷል፡፡
ኮሚሽኑ በሀገራችን የተከሰቱ ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ የአደጋ ስጋቶችን ቀድሞ በመከላከል፣ መቀነስ፣ ተጎጂ ዜጎችን በመደገፍ እና መልሶ በማቋቋም ረገድ ያሳየው ትጋትና ወገናዊ አንዲሁም ሀላፊነት የሚያበረታታ ቢሆንም ኮሚሽኑ ውስጥ ለሚሰሩት ሰራተኞች ተገቢውን የአገልግሎት ክፍያ እና ምቹ የሥራ ሁኔታ ከመፍጠር አኳያ ኮሚሽኑ በጥናት ላይ የተደገፈ እቅድና አሰራር ዘርግቶ ወደ ስራ መግባት እንደለበት አሳስቧል፡፡
ኮሚቴው በብሔራዊ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ውስጥ በሚተዳደሩ የአዳማና ሻሸመኔ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ምልከታ ባደረግበት ወቅት የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የሰላም ንዑስ ኮሚቴ ሰብሰቢ የተከበሩ ወ/ሮ ብርቱኳን ሰብስቤ እንደገለጹት በኮሚሽኑ ውስጥ ለሚሠሩ ሰራተኞች ተገቢውን የአገልግሎት ክፍያና ጥቅማጥቅም በጊዜው ከመድረስ፣ ምቹ የሆነ የስራ አካባቢን ከመፍጠር፣ ተቋማቱ ዕቅድ ሲያዘጋጁ ፈጻሚዎችን ተሳተፊ ከማድረግ፣ የአቅም ግንባታ ስልጠናዎች ሂደት ውጤታማነት ከመገምገም አንጻር ክፍተት መኖሩን ጠቅሰው በሰራተኞቹ ውስጥ ያለው የመረጃ ቅብብሎሽም መታረም እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡
የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባል የተከበሩ ወ/ሮ ትዕግስት አለማየሁ በበኩላቸው በተቋማቱ ያለው የንብረት አስተዳደርና አያያዝ ሁኔታ እንዲሁም የሰራተኞች ለስራው ያላቸው ቁርጠኝነት የሚያበረታታ ነው ያሉ ሲሆን አሁንም በመጋዘኖቹ የሚገኙ ጊዜ ያለፈባቸው ኬሚካሎች እና የሚወገዱ ንብረቶች በጊዜ አለማስወገድ የሰራተኛውን ጤና አደጋ ላይ የሚጥሉ በመሆናቸው ኮሚሽኑ ትኩረት ሰጥቶ ሊሰራባቸው እንደሚገባ ነው ያስገነዘቡት።
ከሰራተኞች ቅጥር፣ ምደባ፣ እድገት እና ሽኝት ጋር ተያይዞ በኮሚሽኑ ሰራተኞች ዘንድ የሚነሱ ቅሬታዎች እንዳሉ ጠቅሰው የኮሚሽኑ አመራር አካላትና በተዋረድ የሚገኙ የስራ ሀላፊዎች ተቀራርበው በጥናት ላይ የተመሰረተ መመሪያ እና ደንብ በማዘጋጀት ለቅሬታዎቹ ህጋዊና ተገቢ ምላሽ መስጠት እንደለባቸው የቋሚ ኮሚቴው አባላት አሳስበዋል።
በብሔራዊ የአደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን የአዳማና የሻሸማመኔ ቅርንጫፍ ስራ አስኪያጆች እንደገለጹት ተቋማቱ ሀገሪቱ እየገጠማት ላለው ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋዎች ምላሽ በመስጠት ረጋድ ከፍተኛ ሚና እንደሚጫወቱ ጠቁመው ነገር ግን ከፌደራል አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ከሚሰጣቸው መመሪያ ውጭ ቅርንጫፎቹ ሰራተኞች የመቅጠር፣ የማሳደግ፣ የማሰናበት እና የመሸኘት ስልጣን እንደሌላቸው አብራርተዋል፡፡
የሰራተኞችን የአገልግሎት ክፍያ፣ ጥቅማ ጥቅም እና ምቹ የሆነ የስራ አካባቢ ከመፍጠር አንጻር ቅርንጫፎቹ የበጀት ክፍተት እንዳለባቸው እና በዚህም የተነሳ የመልካም አስተዳደር ችግር እንደፈጠረባቸው ጠቁመው ኮሚሽኑ ይህንን ከግምት ውስጥ ያስገባ እና ያልተማክለ ስርዓት በሁሉም ቅርንጫፎች በፍጥነት ዘርግቶ በሚመለከታቸው አካላት በማጸደቅ ወደ ስራ ሊገባ እንደሚገባም አክለው ተናግረዋል፡፡
በሚፍታህ ኪያር
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives