የምክር ቤቱ የሕግ አወጣጥ፣ የክትትልና ቁጥጥር ሥራዎችን እየተጠናከሩ መምጣታቸው ተገለፀ
የምክር ቤቱ የሕግ አወጣጥ፣ የክትትልና ቁጥጥር ሥራዎችን እየተጠናከሩ መምጣታቸው ተገለፀ
(ዜና ፓርላማ) ሰኔ 30 ቀን፣ 2017 ዓ.ም፤ የምክር ቤቱ የሕግ አወጣጥ፣ የክትትልና ቁጥጥር ሥራዎች እየተጠናከሩ መምጣታቸውን የምክር ቤቱ ምክትል አፈ-ጉባኤ የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ በዶ ባቀረቡት የምክር ቤቱን የ2017 በጀት ዓመት የተጠቃለለ የዕቅድ ክንውን ሪፖርት ገልፀዋል፡፡
የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ በምክር ቤቱ የአሰራርና የአባላት ስነ-ምግባር ደንብ ቁጥር 6/2008 አንቀጽ 53 (4) መሠረት ረቂቅ ህጎች ለዝርዝር ምርመራ የተመራላቸው የቋሚ ኮሚቴ አባላት ከህግ ምርመራ መሠረታዊ ነጥቦች አንጻር በተገቢ ሁኔታ መመርመር መቻላቸውን አብራርተዋል፡፡
በበጀት ዓመቱ ወደ ምክር ቤቱ የመጡ ረቂቅ አዋጆች በዋናነት ከሕገመንግሥቱ ጋር የተጣጣሙ መሆናቸው፣ ሕጎቹ በተፈለጉበት ጉዳይ ላይ ፖሊሲ ወይም ስትራቴጂ መኖሩና በረቂቁ ውስጥ በአግባቡ መካተቱን የማረጋገጥ፣ ኢትዮጵያ የፈረመቻቸውንና ያፀደቀቻቸውን ዓለም አቀፍ ህጎችና ስምምነቶች ጋር የተናበቡ መሆናቸው መታየቱን ገልፀዋል፡፡
በተጨማሪም የአካል ጉዳተኞችን፣ የአረጋውያንን፣ የሴቶችንና የሕፃናትን መብት የሚያስከበሩ መሆኑን፣ በመሠረታዊነት ተግባራዊ ሊደረጉ የሚችሉ እና ተፈጻሚ የሚያደርጋቸው አካላት መኖራቸውን በማረጋገጥ ሂደታቸውን ጠብቀው እንዲፀድቁ የማድረግ ሥራዎች መሰራታቸውንም የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ አክለዋል፡፡
በዚህ መሠረት በበጀት ዓመቱ ምክር ቤቱ ባካሄደው 43 መደበኛ ስብሰባዎችና 3 ልዩ ስብሰባዎች 56 አዋጆች ለምክር ቤቱ የቀረቡ ሲሆን ከነዚህም 34 ለቋሚ ኮሚቴዎች ተመርቶ ይፋዊ የሕዝብ ውይይት ተደርጎ በሁለተኛ ንባብ ሲፀድቁ 15 ወደ ሁለተኛ ንባብ ተሸጋግሮ መፅደቃቸውን እና ከ2016 የተሸጋገሩትን 2 አዋጆችን ጨምሮ በአጠቃላይ 9 አዋጆች ወደ 2018 በጀት ዓመት መሻገራቸውን አብራርተዋል፡፡
የክትትልና ቁጥጥር ሥራዎችን በተመለከተ በምክር ቤቱ መክፈቻ ላይ ክቡር የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ፕሬዚዳንት ለምክር ቤቱ ያቀረቡትን ንግግር ለማጽደቅ በመንግስት ተጠሪ ሚኒስትር ሞሽን ቀርቦ በቀረበው የመንግስት ሞሽን ላይ የምክር ቤት አባላት ያላቸውን ጥያቄ አቅርበው በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቶበት ሞሸኑም በም/ቤቱ መፅደቁንም በሪፖርታቸው አመላከክተዋል፡፡
ምክር ቤቱ በቋሚ ኮሚቴዎቹ በኩል የፌዴራል መንግስት አስፈጻሚ እና ሌሎች ለምክር ቤቱ ተጠሪ የሆኑ ተቋማትን የክትትልና ቁጥጥር ተግባር በማከናወን የ2017 በጀት ዓመት ዕቅድ በመገምገም ተቋማቱ በቀጣይ ትኩረት ሰጥተው ሊሰሩባቸው ይገባል ያሉዋቸውን ተግባራት በማስቀመጥ በፅሑፍ ግብረ-መልስ እንዲደርሳቸው መደረጉንና በግብረ-መልሱ መሠረት ዕቅዳቸውን ከልሰው እንዲልኩም ተደርጓል ብለዋል፡፡
የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ አያይዘውም በክቡር በጠቅላይ ሚኒስትሩ ከቀረበው የፌዴራል መንግስት የ6 ወራት አፈጻጸም ሪፖርትን ጨምሮ የአስፈጻሚ ተቋማት ሚኒስትሮች በምክር ቤቱ በአካል በመገኘት የስድስት፣ የዘጠኝ እና 11 ወራት የዕቅድ ክንውን ሪፖርት እንዲያቀርቡና ከአባላትና ከሕዝቡ በተነሡ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ላይ ምላሽና ማብራሪያ እንዲሰጡ መደረጉንም አብራርተዋል፡፡
በምክር ቤቱ መደበኛ ጉባኤ ላይ በመገኘት ሪፖርት ካቀረቡት ውስጥም የኢንዱስትሪ፣ የግብርና፣ የከተማና መሠረተ ልማት፣ የገቢዎች፣ የትምህርት፣ የሥራና ክህሎት፣ የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ እና የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር በዋናነት እንሚገኙበት አንስተዋል፡፡
ምክር ቤቱም በአፈጻማቸው ላይ በተለይም መሻሻል በሚገባቸው አንኳር ጉዳዮች ላይ አቅጣጫዎችን ማስቀመጡንም ነው ተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ ባቀረቡት ሪፖርት ያመላከቱት፡፡
በተጨማሪ የውኃና ኢነርጂ ሚኒስቴርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በጥያቄ ክፍለ ጊዜ ከአባላት ለሚነሱ ጥያቄዎች በአካል በመገኘት ምላሽና ማብራሪያ መስጠታቸውን፣ የፌደራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የአስፈፃሚ መሥሪያ ቤቶች የ2016 የኦዲት ግኝትን አስመልከቶ ሪፖርቱን ለምክር ቤቱ በማቅረብ ውይይት የተደረገበት መሆኑንም ገልጸዋል፡፡
ምክር ቤቱ በሚያከናውናቸው የክትትልና ቁጥጥር ሥራዎች የዕቅድ አካል በማድረግ ተገቢውን ክትትል የማድረግ እና የማስተካከያ እርምጃዎችን በማይወስዱ ተቋማት ላይ ደግሞ ተጠያቂነትን የማስፈን ሥራዎች መሠራት እንዳለበት አቅጣጫ አስቀምጧልም ብለዋል፡፡
የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ የገንዘብ ሚኒስቴር የፌደራል መንግስት የ2018 በጀት ላይ ለምክር ቤቱ በበጀቱ አዘገጃጀትና ይዘት ላይ በጹሁፍ ማብራሪያ ማቅረቡንና ክቡር ሚኒስትሩም በዝርዝር ለቀረበላቸው ጥያቄዎችም ምላሽና ማብራሪያ መስጠታቸውንም አስረድተዋል፡፡
የፌዴራል መንግስት የ2017 አፈፃጸም ሪፖርትና የ2018 በጀት ዕቅድ እንዲሁም በሀገሪቱ አጠቃላይ ጉዳዮች ላይ ከምክር ቤት አባላት በሚቀርቡ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ክቡር የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በምክር ቤቱ ተገኝተው ምላሽና ማብራሪያ መስጠታቸውን እና የፌደራል መንግስት 2018 በጀት ዓመት በጀት በዝርዝር ተመርምሮ መፅደቁንም ተናግረዋል፡፡
ቋሚ ኮሚቴዎች በከተማና በክልሎች በተናጠልና በቅንጅት የመስክ ምልከታ ሥራዎች ማከናወናቸውንም አስረድተዋል፡፡
በመጨረሻም የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ በዶ በአጠቃላይ በ13 ቋሚ ኮሚቴዎች በአስፈፃሚ ተቋማት ላይ የ2017 በጀት ዓመት የተደረገው የክትትልና ቁጥጥር ስራ ከዕቅድ በላይ መፈጸሙን ገልፀዋል፡፡
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives