የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ከጎረቤት ሀገራት ብቻ ሳይሆን ከተለያዩ ቀጠናዊ ኃይሎች ጋር በጋራ እንሰራለን
"የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ከጎረቤት ሀገራት ብቻ ሳይሆን ከተለያዩ ቀጠናዊ ኃይሎች ጋር በጋራ እንሰራለን"
------ ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ------
(ዜና ፓርላማ) ግንቦት 28፣ 2017 ዓ.ም፤ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ከጎረቤት ሀገራት ብቻ ሳይሆን ከተለያዩ ቀጠናዊ ኃይሎች ጋር በጋራ እንደሚሰራ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ተናገሩ፡፡
ዛሬ በተካሄደው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 34ኛ መደበኛ ስብሰባ፤ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ከምክር ቤቱ አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
የምክር ቤቱ አባላት የተለያዩ ጥያቄዎች ላይ ማብራሪያ የጠየቁ ሲሆን፤ ኤርትራን ጨምሮ ከተለያዩ የጎረቤት ሀገራት ጋር ያለው ግንኙነት፣ በውጭ ሀገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያዊያንን መብት ለማስጠበቅና ከተለያዩ አደጋዎች ለመታደግ የሚደረገው ጥረት፣ በድንበር አከባቢ የሚሰፍሩ የጎረቤት ሀገራት ህዝቦች እና በውጭ ኃይሎች የተያዙ የኢትዮጵያ ግዛቶችን በሚመለከት የተነሱት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡
የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ኢትዮጳያ ለጎረቤት ሀገራት ቅድሚያ የመስጠት ዲፕሎማሲያዊ መርህ እንዳላት ጠቁመው፤ ይሁን እንጂ የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ ከተለዩ ቀጠናዊ ኃይሎች ጋር የሚሰራው ስራም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አብራርተዋል፡፡
ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ ሰላምና መረጋጋት እንዲረጋገጥ ለቀጣናው ኢኮኖሚ ትስስር መጠናከር ወሳኝ ሚና የምትጫወት ሀገር ስለመሆኗ በተለያዩ አለም አቀፍ መድረኮች እየተረጋገጠ ስለመሆኑም አንስተዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ መንግስት ከኤርትራ ጋር የቃላት ጦርነት ውስጥ አለመግባቱንና የባህር በር ጥያቄን ለማሳካት የተጀመረው ዲፕሎማሲያዊ አካሄድ እውን እስኪሆን ድረስ በዓለም አቀፍ ህጎች እና በሰጥቶ መቀበል መርህ መስራት እንደሚገባም አመላክተዋል።
በኢትዮጵያ እና በኤርትራ መካከል ያለው ህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ከመንግስታት ግንኙነት የላቀ ትርጉም ያለው በመሆኑ በቀጣይም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጌዲዮን (ዶ/ር) አንስተዋል፡፡
በሌላ በኩል በህገ ወጥ መንገድ ከሀገር የሚወጡ ዜጎችን ወደ ሀገር ቤት በመመለስ፣ በህጋዊ መንገድ በውጭ ሀገራት የሚሰሩ ዜጎችን መብት በማስጠበቅ እየተሰሩ ያሉት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ገልጸው፤ ነገር ግን በህገ ወጥ መንገድ ከሀገር የመውጣቱ ጉዳይ አሁንም ፈታኝ እንደሆነባቸው አስረድተዋል፡፡
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives