የ2018 በጀት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል ምክር ቤቱ አሳሰበ
የ2018 በጀት ለታለመለት ዓላማ እንዲውል ምክር ቤቱ አሳሰበ
(ዜና ፓርላማ) ሰኔ 03 ቀን ፣ 2017 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፣ ባለበጀት መስሪያ ቤቶች የሚመደብላቸውን በጀት ለታለመለት ዓላማ እንዲያውሉ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ክትትልና ቁጥጥር ማድረግ እንዳለበት የምክር ቤት አባላት አስገንዝበዋል፡፡
ክቡር ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሽዴ የ2018 ዓ.ም ረቂቅ በጀት መግለጫ (Budget speech) ለምክር ቤቱ በዝርዝር አቅርበዋል፡፡
በጀቱ የመካከለኛ ዘመን ማይክሮ ኢኮኖሚ ዕድገትን ታሳቢ በማድረግ፤ ለዕዳ ቅነሳና ለዋጋ ንረት በረቂቅ አዋጁ ልዩ ትኩረት የተሰጠው መሆኑን ክቡር ሚንስትሩ ገልጸዋል፡፡
በበጀት ዓመቱ መንግስት ከብሔራዊ በባንክ ገንዘብ ሳይበደር ማጠናቀቅ መቻሉ የፋይናንስ ውጤታማነትን አንዱ ማሳያ መሆኑን ክቡር ሚኒስትሩ ጠቁመው፤ በቀጣይ ዓመትም የተጀመሩ የልማት ስራዎች እንዲጠናቀቁና የተረጋጋ የማይክሮ ኢኮኖሚ ለመገንባት ታሳቢ ያደረገ ረቂቅ በጀት መሆኑን አብራርተዋል፡፡
የሀገር ውስጥ ገቢን በማሳደግና በማጠናከር ጤናማ የፋይናንስ ስርዓትን በመፍጠር ዘላቅ የልማት ግቦችን ለማከናወን በረቂቅ አዋጁ በእቅድ የተያዘ መሆኑን ክቡር ሚኒስትሩ ጠቁመዋል፡፡
አዲስ በተዋቀሩ ክልሎች ከበጀት ጋር በተያያዘ እያጋጠመ ያለውን ችግር ለመቅረፍ የውስጥ የፋይናንስ አቅም በማጠናከር እና ያለውን የሰራተኛ አደረጃጀት በመፈተሽ አሰራሮችን ማረምና ማስተካከል እንደሚገባ ክቡር ሚኒስትሩ አያይዘው አስገንዝበዋል፡፡
በህዝቡ ዘንድ እየተነሱ ያሉት የመሰረት ልማት ፍላጎቶች በርካታ በመሆናቸው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ በረቂቅ አዋጁ ለፕሮጀክቶች ተፈፃሚነት ታሳቢ ማድረግ እንዳለበት የምክር ቤት አባላት አሳስበዋል፡፡
ከዋጋ ንረት፣ በግጭት የተጎዱ ተቋማት እና የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች ተፈፃሚነትን ለማረጋገጥ በሚያስችል መልኩ ረቂቅ አዋጁ የሚመራለት ቋሚ ኮሚቴ ማየት እንዳለበት የምክር ቤቱ አባላት አመላክተዋል፡፡
ምክር ቤቱም በረቂቅ በጀቱ ላይ ከተወያየ በኋላ ለዝረዝር ዕይታ ለበጀት፣ ፕላን እና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መርቷል፡፡
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives