(ዜና ፓርላማ)፤ ሐምሌ 4፣ 2014 ዓ.ም.፤ ቢሾፍቱ፤ “ዴሞክራሲ ለኢትዮጵያ የምርጫ ጉዳይ ሳይሆን፤ ጠንካራ፣ የተረጋጋች ሰላማዊ ሀገር የመገንባት ጉዳይ ነው" ሲሉ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር የተከበሩ አቶ ተስፋዬ በልጅጌ ተናገሩ፡፡

ዋና ተጠሪው ይህንን የተናገሩት፤ ምክር ቤቱ ከዴሞክራሲ ተቋማት ጋር እያካሄደ በሚገኘው የጋራ ፎረም ላይ በሰጡት አስተያየት ነው፡፡

የዴሞክራሲ ተቋማት ግንባታ የዴሞክራሲ ባሕል ግንባታ ስራ መሆኑን በዚሁ አስተያየታቸው ያመላከቱት የተከበሩ አቶ ተስፋዬ፤ ገለልተኛ የዴሞክራሲ ተቋማትን ለመገንባት የተጀመረዉ ሥራ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ብለዋል፡፡

“ኢትዮጵያዊ የሆኑ ጠንካራ ተቋማትን ለመገንባት የሁሉም ባለድርሻ አካላት ትኩረት ወሳኝ ነው፡፡ ለአብነትም በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን እና በዕንባ ጠባቂ ተቋም በኩል ለውጥ ለማምጣት ታልመው የተከናወኑት ሥራዎች አበረታች ናቸው” ዋና ተጠሪ ሚኒስትሩ እንዳስረዱት፡፡

የሰብዓዊ መብት እና የዕንባ ጠባቂ ተቋም የሪፎርም ሥራዎች አተገባበር እና ተቋማቱን ለማጠናከር የተሠሩ ሥራዎች እንዲሁም ጥንካሬ እና ድክመቶች ተለይተው፤ ለጋራ ፎረሙ ቀርበዋል፡፡ በተሳታፊዎችም ውይይት እየተደረገባቸው እንደሆነ ከስፍራው የደረሰን መረጃ ያመላክታል፡፡