ኢትዮጵያ ከኢራን ሪፐብሊክ መንግስት ጋር ያላትን ግንኙነት ይበልጥ የማጠናከር ፍላጎት እንዳላት አፈ-ጉባኤው ገለጹ
ኢትዮጵያ ከኢራን ሪፐብሊክ መንግስት ጋር ያላትን ግንኙነት ይበልጥ የማጠናከር ፍላጎት እንዳላት አፈ-ጉባኤው ገለጹ
(ዜና ፓርላማ) ጥር 9 ቀን፣ 2017 ዓ.ም.፤ አዲስ አበባ፤ ኢትዮጵያ ከኢራን ጋር ያላትን ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት የበለጠ የማጠናከር ፍላጎት እንዳላት የተከበሩ አፈ-ጉባኤ አቶ ታገሰ ጫፎ ገለጹ።
አፈ ጉባኤው በተከበሩ ዶ/ር መሐመድ ጋሊባፍ (ዶ/ር) ከሚመራው የፓርላማ ልዑካን ቡድን ጋር በሁለቱ ወዳጅ ሀገራት በሀገራዊና ፓርላሜንታዊ ዲፕሎማሲያዊ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት አድርገዋል።
የተከበሩ አፈ-ጉባኤ አቶ ታገሰ ኢትዮጵያ እና ኢራን ጋር ረጅም ዘመናትን ያስቆጠረ፣ በወዳጅነትና በመከባበር ላይ የተመሰረተ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ለዚህም በ1960ዎቹ ኢትዮጵያ በኢራን ቆንፅላ መክፈቷን በማሳያነት አንስተዋል፡፡
ኢትዮጵያ በኢኮኖሚ በማደግ ላይ ያለች እና በርካታ የህዝብ ቁጥር ያላት ሀገር ናት ያሉት አፈ-ጉባኤው በቀጣይም ሁለቱ ሀገራት በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ አብረው በመስራት ግንኙነታቸውን ይበልጥ ማጠናከር እንዳለባቸውም ነው የተከበሩ አፈ-ጉባኤው የጠቆሙት፡፡
የኢራኑ አፈ-ጉባኤ ዶ/ር መሐመድ ጋሊባፍ በበኩላቸው ሁለቱ ሀገራት ረጅም ዘመን ያስቆጠረ ታርክ እና ባህል ያላቸው ሀገራት መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡
በቀጣይም ሀገራቸው ኢትዮጵያ የጀመረችውን የኢኮኖሚ እድገት ለማጠናከር በኢኮኖሚ፣ በቴክኖሎጂ እና በንግድ አማራጮች በመደገፍ ወዳጅነቷን አጠናክራ እንደምትቀጥልም አስረድተዋል፡፡
የተከበሩ አፈ-ጉባኤ መሐመድ ጋሊባፍ (ዶ/ር) ለልዑካን ቡድኑ የኢትዮጵያ መንግስት እና ፓርላማው ላደረገላቸው አቀባበል በሀገራቸው ኢራን፣ በልዑካኑ ቡድኑ እና በራሳቸው ስም ማመስገን እንደሚፈልጉ ገልጸዋል፡፡
በመጨረሻም አፈ ጉባኤዎቹ በምክር ቤቱ ቅጥር ግቢ ውስጥ የመታሰቢያ ችግኝ የመትከል ስነስርዓት አካሂደዋል።
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives