6ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለማከናወን የለውጥ ስራዎች መሰራታቸው ተገለጸ
6ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለማከናወን የለውጥ ስራዎች መሰራታቸው ተገለጸ
(ዜና ፓርላማ ) ፣ ሚያዝያ 25 ፣ 2013 ዓ.ም ፤ አዲስ አበባ ፣ 6ኛውን ሀገራዊ ምርጫ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለማከናወን በርካታ የለውጥ ስራዎች መከናወናቸውን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ የተከበሩ ታገሠ ጫፎ ገለጹ ፡፡
አፈ-ጉባኤው ይህንን የገለጹት የስድስተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ቅድመ-ዝግጅት አስመልከቶ ከአፍሪካ ሕብረት የምርጫ ታዛቢዎች ጋር በጽ/ቤታቸው በተወያዩበት ወቅት ነው ፡፡
ምርጫው ነጻ፣ፍትሃዊና ተዓማኒ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች በተሳተፉበት መንገድ የምርጫ ሕጉ መሻሻሉንና የምርጫ ቦርድ አባላት መመረጣቸውን ለታዛቢዎቹ አብራርተውላቸዋል ፡፡
ምርጫው በተቀመጠለት የጊዜ መርሃ-ግብር እንዲከናወን ለማድረግ የምርጫ ቁሳቁሶች ወደየምርጫ ጣቢያዎች እንደተጓጓዙ የጠቀሱት አፈ-ጉባኤው ፣ በምርጫው ሂደት የሚያጋጥሙ ችግሮችን ለመፍታት ሕጋዊ አሰራሮችና የጸጥታ አደረጃጀቶች እንደተዘረጉም ነው የተናገሩት ፡፡
በጸጥታ ጉዳይ በአንዳንድ የሀገሪቷ አካባቢዎች ተራዝሞ የነበረው የመራጮች ምዝገባም በአሁኑ ጊዜ ከሞላ ጎደል መጠናቀቁን የተናገሩት አፈ-ጉባኤ ታገሠ ፤ ምርጫው ነጻ፣ ፍትሃዊና ተዓማኒ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ታዛቢ ቡድኑ በቂ መረጃ ማግኘቱን አፈ-ጉባኤው አረጋግጠዋል ፡፡
በምርጫው የሴቶችን ተሳትፎ ከፍ ለማድረግና ሴቶች መራጭ ብቻ ሳይሆኑ ተመራጭም እንዲሆኑም መንግስት በትኩረት ስራዎችን እያከናወነ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ታገሠ ፣ በአሁኑ ጊዜ በአመራር ሰጭነት የሴቶች ተሳትፎ 50 በመቶ መሆኑንም አስረድተዋል ፡፡
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives