የሕዝብ ተወካዮች ምክር የፌዴራል መንግሥትን የ2019 በጀት 2.3 ትሪሊዮን ብር አድርጎ አፀደቀ
-----------------------
(ዜና ፓርላማ) ሰኔ 30፣ 2018 ዓ.ም፤ የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው 30ኛ መደበኛ ስብሰባው የ2019 በጀትን በሙሉ ድምፅ አፅድቋል።
ምክር ቤቱ የ2019 በጀት ዓመት የፌደራል መንግስት ረቂቅ በጀት ላይ ከተወያየ በኋላ የቀረበውን የ2.339 ትሪሊዮን ብር በጀት በአዋጅ ቁጥር 1437/2018 አድርጎ በሙሉ ድምፅ አፅድቋል።
በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ ደሳለኝ ወዳጄ የውሳኔ ሃሳብ እና ሪፖርት አቅርበዋል፡፡
ከተያዘው አጠቃላይ በጀት ውስጥ 1.49 ትሪሊዮን ብሩ ከታክስ ገቢ የሚሰበሰብ ሲሆን፣ ቀሪው የ93.7 ቢሊዮን ብር ከልማት አጋሮች በሚገኝ ብድርና ድጋፍ እንዲሁም 320 ቢሊዮን ብር ከሀገር ውስጥ በሚገኝ ብድር የሚሸፈን መሆኑን ሰብሳቢው አስረድተዋል፡፡
አጠቃላይ የበጀት ጉድለቱ ከጠቅላላው የሀገራዊ ምርት (GDP) ያለው ድርሻ 1.4 በመቶ ብቻ መሆኑ ማክሮ ኢኮኖሚን ለማረጋጋት የተያዘውን የፖሊሲ አቅጣጫ የሚያሳይ መሆኑም የተከበሩ አቶ ደሳለኝ ወዳጄ ገልጸዋል፡፡
በበጀት ድልድሉ 30 በመቶ የሚሆነው ከፍተኛው ድርሻ ለትምህርት፣ ለመንገድ፣ ለጤና፣ ለግብርና፣ ለኃይል አቅርቦት ማስፋፊያ እና ለከተማ ልማት የተመደበ ሲሆን፣ ለክልሎች የበጀት ድጋፍ 187.3 ቢሊዮን ብር ወይም 15.1 በመቶ ተመድቧል።
ይህም ከባለፈው ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ28.4 ቢሊዮን ብር ወይም 17.8 በመቶ ጭማሪ እንደሚያሳይ ተመላክቷ።
የምክር ቤት አባላት በበኩላቸው፤ ባለበጀት መስሪያ ቤቶች የሚመደብላቸውን በጀት በላቀ ውጤታማነት እና ለታለመለት ዓላማ በማዋል በኃላፊነት ስሜት ሊፈጽሙ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
የሚመደበውን በጀት ለታለመለት ዓላማ መዋሉን የክትትል እና የቁጥጥር ስራዎችን ማጠናከር እንደሚገባ የምክር ቤት አባላት አይይዘው አስገንዝበዋል፡፡
(በመኩሪያ ፈንታ)
ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/@FDREHOPR
በቴሌግራም
በትዊተር
በዌብሳይት
www.hopr.gov.et ይከታተሉ።