null “Arba-Minch University shall stand peace model”

የአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ሰላማዊ የመማር ማስተማር እንቅስቀሴ በተሞክሮነት ሊወሰድና ተጠናክሮ ሊቀጥል የሚገባው እንደሆነ ተገለጸ 

ይህ የተገለጸው በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሰው ሃብትና ቴክኖሎጅ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰሞኑን በአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የመስክ ምልከታ ባደረገበት ወቅት ነው፡፡

የዩኒቨሲቲው ፕሬዘዳንት ዶ/ር ዳምጠው ዳርዛ የተቋሙን የስራ እንቅስቃሴ አስመልክተው ለቋሚ ኮሚቴው ገለጻ ባደረጉበት ወቅት ሰላማዊ የመማር ማስተማር ስራውን ማስፈን ትኩረት የተሰጠው ተግባር እንደሆነ አስታውሰው ይህንንም ማሳካት የቻልነው ከአካባቢው ማህበረሰብ፣ ከሃይማኖት አባቶች፣ ከጸጥታ አካላትና ከተማሪዎች አደረጃጀቶች ጋር ተቀራርበን በመስራታችን ነው ብለዋል፡፡

ለተማሪዎች የሚሰጡ አገልግሎቶችን ከማሟላት አኳያ ዩኒቨርሲቲው ተገቢውን ጥረት እያደረገ መሆኑን የገለጹት ፕሬዘዳንቱ ነገር ግን ለአንድ ተማሪ ቀለብ ተብሎ በቀን የተመደበው 15 ብር የወቅቱን የገበያ ሁኔታ ግምት ውስጥ ያላስገባና ፍትሃዊ ያልሆነ በሆመኑ የሚመለከተው አካል ትኩረት ሰጥቶ ሊፈታው ይገባል በማለት ተናግረዋል፡፡

ውጤታማ ጥናትና ምርምር ከማካሄድና የማህበረሰቡን ህይወት ከማሻሻል አኳያ በእንስሳት በሽታ፣ በደጋ ፍራፍሬና በአሳ እርባታ እንዲሁም ቴክኖሎጅዎችን በማሸጋገር ረገድ ትኩረት ተደርጎ እየተሰራ መሆኑን የጠቆሙት ዶ/ር ዳምጠው በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እና በቴክኒክና ሙያ ማስልጠኛ ኮሌጆች ላይም ሙያዊ ድጋፍ እየተደረገ እንደሆነም አመላክተዋል፡፡

የተማሪዎች በጀት ከወቅቱ የገበያ ሁኔታ ጋር አለመመጣጠን፣ የተሸከርካሪ እጥረት፣ የመምህራን መኖሪያ ቤት እጥረት የመሳሰሉት ለመማር ማስተማር ስራው እንቅፋት የሆኑ ቁልፍ ችግሮች በመሆናቸው መንግስት ትኩረት ሰጥቶ ሊፈታልን ይገባል ሲሉ የዩኒቨርሲቲው አመራሮች በአጽንኦት አንስተዋል፡፡

ቋሚ ኮሚቴው በበኩሉ በማጠቃላያ አስተያየቱ እንዳለው የዩኒቨርሲቲው አመራር የመማር ማስተማር ስራው ሰላማዊ ሆኖ እንዲቀጥል ለማድረግ ከአካባቢው ማህበረሰብ፣ ከሃይማኖት አባቶች፣ ከጸጥታ አካላትና ከተማሪዎች አደረጃጀቶች ጋር ተቀራርቦ መስራቱ በጥንካሬ የሚወሰድ ተግባር መሆኑን አንስቶ የተማሪዎች አገልግሎትን በማሟላት ትምህርታቸው ላይ ብቻ እንዲያተኩሩ ለማድረግ እተከናወነ ያለው ተግባር በተሞክሮነት የሚወሰድና ተጠናክሮ ሊቀጥል የሚገባው እንደሆነም አስገንዝቧል፡፡

አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ላብራቶሪና የወርክ ሾፖች አደረጃጀቶች ዘበናዊና ለአገር እድገት ተስፋ የሚጣልባቸው መሆኑን የገለጸው ቋሚ ኮሚቴው መንግስት የዚህን ተቋም እምቅ አቅም አሟጦ ሊጠቀምበት ይገባል በማለት አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡

የዩኒቨርሲቲ-ኢንዱስትሪ ትስስሩ የተጠናከረ መሆኑ ተማሪዎች በንድፈ-ሃሳብ ያገኙትን እውቀት በተግባር እንዲያጠናክሩት ከማስቻሉም ባሻገር እንዱስትሪዎችም የሰለጠነ ባለሙያ ፍላጎታቸውን ማሟላት እንዲችሉ እና ተወዳዳሪነታቸውን እንዲያሳድጉ ስለሚያግዝ ተጠናክሮ መቀጠል ያለበትና በመተሞክሮንት ሊወሰድ የሚገባው ተግባር እንደሆነም አስገንዝቧል፡፡

ዩኒቨርሲቲው የተጣለበትን አገራዊ አደራ በብቃት ሊወጣ የሚችለው መሰረታዊ የሚባሉ ግብዓቶች በበቂ መጠንና በወቅቱ ሲቀርቡለት እንደሆነ ያስታወሰው ቋሚ ኮሚቴው በተለይ ከተሸከርካሪ፣ ከግዥ መጓተት፣ ከተማሪዎች ቀለብ አቅርቦት፣ ከግንባታ መጓተትና ከወሰን ማስከበር ጋር ያሉ ቁልፍ ችግሮች በመንግስት በኩል ሊፈቱለት ይገባል ብሏል፡፡

የፌደራል ዋና ኦዲተር የኦዲት ግኝትን ለማስተካከል እየተደረገ ያለው ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል እንዳለበትና ከአቅም በላይ የሆኑ ጉዳዮች ካሉም ከእነ አሳማኝ ምክንያታቸው ለሚመለከተው አካል በወቅቱ መቅረብና መፈታት አለባቸው ሲልም ቋሚ ኮሚቴው አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡

የአካባቢው የአርሶ አደር ምርትና ምርታማነት ችግር ፈች በሆነ ምርምር መደገፍ እንዳለበት የጠቆመው ቋሚ ኮሚቴው የምርምር ስራው በጤናውም ዘርፍ ትኩረት ማድረግ አለበት ሲልም አሳስቧል፡፡

ዘጋቢ:- ድረስ ገብሬ