null Committee of the House said that 1034 illegal agents have taken action.

በ1034 ህገ-ወጥ  ኤጀንሲዎች ላይ እርምጃ መወሰዱ ተገለጸ፡፡

ግንቦት 15 ቀን 2011 ዓ.ም፤ በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሴቶች ፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ  ቋሚ ኮሚቴ  በአሰሪና   ሰራተኞች መካከል   ያለውን ግንኙነት አስመልክቶ በአዲስ አበባ ከተማ   የመስክ ምልክታ አደርጓል፡፡

ቋሚ ኮሚቴው  የኢፌዲሪ ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዶ.ር ኤርጎጌ ተስፋዬን ጨምሮ የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በምልከታው የተገኙ ግኝቶችን አቅርቧል ፡፡

የውጭ ሃገራት የስራ ስምሪት አዋጅ በተለያዩ ምክንያቶች ለአራት አመታት  ወደ ስራ መግባት አለመቻሉን ፣ የሃገር ውስጥ ስራና ሰራተኛ በማገናኘት አገልግሎት ላይ የተሰማሩ ኤጀንሲዎች የህገ-ወጥነት መስፋፋት ፣ የፌደራል የአሰሪና ሰራተኞች አማካሪ ቦርድ ተጠናክሮ ወደ ስራ አለመግባት ቋሚ ኮሚቴው   በምልከታው ካገኛቸው ግንቶች ተጠቃሾች መሆናቸውን ገልጿል፡፡

ቋሚ ኮሚቴው ባደረገው ክትትል ያለ ፈቃድ ሲሰሩ ባገኛቸው 1034 ህገ-ወጥ ኤጀንሲች ላይ እርምጃ እንደተወሰደ ተናግሯል፡፡

 ኤጀንሲዎች የውሸት ክፍት የስራ ቦታ በማውጣት ከስራ ፈላጊዎች በተለይም ከዲግሪ ምሩቃን ከብር 400 እስከ 8000 እንደሚቀበሉ ተደርሶበት ፈቃድ የመሰረዝ ስራ እንደተሰራ ተናግሯል፡፡

ለአብነትም የኔታ  በሃገር ውስጥ ስራና ሰራተኛ አገናኝ ኤጀንሲ ፣ ኤ.ዲ በሃገር ውስጥ ስራና ሰራተኛ አገናኝ ኤጀንሲ እንዲሁም GOS Plan Trading ተጠቃሽ ናቸው ብሏል፡፡

ከስራ ፈላጊዎች ብር የተቀበሉት ኤጀንሲዎች ከፈቃድ ስረዛው ባሻገር ወደ ህግ ቀርበው እንዲጠየቁ የማድረግ ስራ ሊሰራ እንደሚገባም ቋሚ ኮሚቴው  አብራርቷል ፡፡

ሰራተኞች  ለሚሰሩት  ስራ ተመጣጣኝ  የሆነ ክፍያ አይከፈላቸውም፤  በዚህም  ምክንያት  ለጉልበት ብዝበዛ እየተዳረጉ እንደሆነ ከወከልነው ህዝብ ጋር በነበረን ውይይት ጉዳዩ ተነስቶ ማረጋገጥ ችለናል ሲል ቋሚ ኮሚቴው  ገልጿል፡፡

ሰራተኞቹ በሃገር ውስጥ አሰሪ ኤጀንሲዎች የሚፈጸምባቸውን ዘመናዊ ባርነት ለመሸሽ  ለህገ-ወጥ ስደት እየተዳረጉ እንደሚገኙም አክሏል፡፡

ለሰራተኞቹ የሚከፈለው ደመወዝ አነስተኛ የሚሆነው አሰሪ ኤጀንሲዎች ቫትን ጨምሮ የተለያዩ ክፍያዎችን ከሰራተኞቹ ደመወዝ ቀናንሰን  ለመንግስት ስለምንከፍል  ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡

በሰራተኞች ላይ ዘመናዊ ባርነት አንፈጽምም  ጉዳዩ በማን እተፈጸመ እንደሆነ ቋሚ ኮሚቴው ክትትል ቢያደረግ እውነታው ላይ መድረስ እንደሚችል ተገልጿል፡፡

ሰራተኞች የመደራጀት መብት ተነፍጎናል ሲሉ በተለያየ ጊዜ ቅሬታ እንደሚያነሱ የሴቶች ፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳይ  ቋሚ ኮሚቴ ወ/ሮ አበባ ዮሴፍ ተናግረዋል፡

ሁሉም አሰሪ ኤጀንሲ መደራጀት መብት መሆኑን አውቀው በመንቀሳቀስ የኢንዱስትሪ ሰላምን ለማስፈን የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ወ/ሮ አበባ አሳስበዋል፡፡

የውጭ ሃገር ስራ ስምሪት  አገልግሎት ሰጪ ኤጀንሲዎች  የውጭ ሃገራት የስራ ስምሪት ከመስከረም 30 ቀን 2011 ዓ.ም ጀምሮ ተከፍቷል በሚል በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በይፋ ከተነገረ በኋላ እስከ ዛሬ ድረስ የአለመጀመሩና ለስራ ወደ ውጭ ሃገር የሚሄዱ ሰራተኞች ቢያንስ የ8ኛ ክፍልን ያጠናቀቁ መሆን ይገባል በሚል መገደቡ ትክክል እንዳልሆነ ቋሚ ኮሚቴው በመስክ ምልከታው ማረጋገጡን ጠቅሷል፡፡

ከሰራተኛ ተቀባይ ሃገራት ጋር የሚደረገው ውይይት  በታሰበው መልኩ መቀጠል አለመቻሉ ለስምሪቱ መዘግየት መንስኤ መሆኑን የሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ.ር ኤርጎጌ ተስፋዬ ተናግረዋል፡፡

ከስምንተኛ ክፍል ጋር ተያይዞ  ለተነሳላቸው ጥያቄም ሰራተኞቹ ማንበብና መጻፍ ችለው መብትና ግዴታዎቻቸውን አውቀው እንዲቀሳቀሱ ታስቦ የተሰራ መሆኑንም  ሚኒስትሯ አክለዋል፡፡

የውጭ ሃገራት የስራ ስምሪት አዋጅ በፍጥነት ወደ ተግባር እንዲገባ የሰራተኛና ማህበረዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን መስራት እንደሚገባው ወ/ሮ አበባ አክለዋል፡፡