null The formal crime investigation commonly known as “Maikelawi” has been closed.

የቀድሞ ማዕከላዊ ወንጀል ምርመራ ተዘግቶ ከቡራዩ የተፈናቀሉ ዜጎች በጊዜያዊነት እየኖሩበት መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግ፣ ፍትህና ዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አረጋገጠ፡፡

ቋሚ ኮሚቴው ታህሳስ 3 ቀን 2011 ዓ.ም ባደረገው የመስክ ምልከታ ማዕከላዊ ስለመዘጋቱ እና በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የሚገኙትን የህግ ታራሚዎችን ተዟዙሮ ጎብኝቷል፡፡

ቀድሞ የማዕከላዊ የተለያዩ ክፍሎች ከቡራዩ ከተማ የተፈናቀሉ የህብረተሰብ ክፍሎች እየኖሩበት መሆኑን ተመልክቷል፡፡ የክሊኒኩን ክፍሎችና የታራሚ ምግብ ማብሰያ ቤቱን የቋሚ ኮሚቴው አባላት ተዘዋውረው የጎበኙ ሲሆን ለአንድ ታራሚ ብቻ ተፈቅደው የነበሩ ጠባብ ክፍሎች ክፍት መሆናቸውንም ታዝበዋል፡፡

በምልከታውም ኮማንደር ኪዳኔ እንደገለፁት ማዕከላዊ ከመጋቢት 28 ቀን 2010 ዓ/ም ጀምሮ መዘጋቱንና በአሁኑ ሰአት ምንም ታራሚ እንደሌለ ገልጸው 139 የፌዴራል ታራሚዎች ወደአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ማረሚያ ቤት በአደራ መልክ መዘዋወራቸውን ተናግረዋል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው አባላት በአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የሚገኙትን ታራሚዎች ተዘዋውረው በጎበኙበት ወቅት ጀነራል ክንፈ ዳኘው፣ ኮሚሽነር ያሬድ ዘሪሁን፣ አቶ ተስፋዬ ኡርጌ እና የቀድሞ ኢትዮ-ሶማሊ ፕሬዚዳንት አቶ አብዲ ኢሊን ጨምሮ ሌሎች ከፍተኛ ታራሚዎች የሰብኣዊ መብት ጥሰት እንደማይደርስባቸው እና የማረሚያ ቤቱ አያያዝና እንክብካቤ ጥሩ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በሌላ በኩል ታራሚዎች የፍትህ መጓተትና የክስ ሂደቱ ውስብስብ መሆኑን ገልጸው  ሚዲያዎች ቀድመው ፍርድ እየሰጡ ነው ሲሉ ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡

ሰሞኑን የተሰራጨው ዶክመንታሪ ፊልም ፍርድ ቤት ውሣኔ ባልሰጠበት ክስ ላይ ትኩረት ማድረጉ ያሳደረብን የሞራል ተፅዕኖ ቀላል አይደለም ሲሉ ለቋሚ ኮሚቴው አባላት ተናግረዋል፡፡