null The standing committees discussed on the immigrant proclamation with concerned stakeholders.

በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የህግ፣ ፍትህና ዴሞክራሲ ጉዳዮች እና የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴዎች በጋራ በተመራላቸው የስደተኞች ጉዳይ አዋጅ ዙሪያ ከሚመለከታቸው ባላድርሻ አካላት ጋር ተወያዩ፣

ስደተኞች ስለሚያሳድሩት የማህበራዊ አገልግሎትና ተፈጥሮ ሃብት ላይ ያላቸውን ጫና፣ ስለሚፈጥሩት ሃብትና ለዜጎቻችን በምንፈጥረው የስራ እድል ላይ የሚያሳድሩትን አሉታዊ ተጽዕኖ የተመለከቱ ጥያቄዎች በውይይቱ ተነስተዋል፡፡

የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታው አቶ ዘይኑ ጀማል በረቂቅ አዋጁ መነሻ ሃሳብና ከአባላት በተነሱ ጥያቄዎች ዙሪያ ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

በማብራሪያቸውም ለስደተኞች የተሻለ ከለላ የሚሰጥና ለችግሮቻቸው ዘላቂ መፍትሄ የሚያስገኝ በአለም አቀፍ መመዘኛዎች መሰረት የተቀረጸ የተሟላ የህግ ማዕቀፍ ባለመኖሩ በስራ ላይ ያሉ ህጎች ተግባራዊ በሚደረጉበት ጊዜ ያጋጠሙ ችግሮችን በመለየት ህጉን ማሻሻል አስፈልጓል ብለዋል፡፡

አገራችን ስደተኞችን ተቀብላ በማስጠላል በኩል ያላት ልምድና ታሪክ የሚያስመሰግን ቢሆንም የተሟላ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶችን እንዲያገኙ በማድረግ በኩል የህግ ክፍተት በመኖሩ ምክንያት ስደተኞች በአገራችን እየተረዱ ከመቀበጥ ውጭ በልማት የሚሳተፉበትና ንብረት የሚያፈሩበት እድል ተነፍጓቸው ቆይተዋል ብለዋል፡፡

በመሆኑም አሉ አቶ ዘይኑ ስደተኞች ጥገኝነት ባገኙበት አገር ከዜጎች እኩል የትምህርትና የስራ እድል የማግኘት እንዲሁም ተደራጅተው የመስራት መብታቸው እንዲከበር ማድረግ የአገርን ገጽታ ከመገንባቱም ባሻገር ከአጎራባችም ይሁን ከአለም አቀፉ ማህበረሰብ ጋር የሚኖረውን የወዳጅነት ግንኙነት ስለሚያጠናክር አገራችንም በተለያየ ጊዜያት የፈረመቻቸውን አለም አቀፍ ስምምነቶች በመመርመርና ከራሳችን ሁኔታ ጋር በማጣጣም ህጉን ማሻሻል ያስፈልጋታል ሲሉ አስረድተዋል፡፡

ስደተኞች ጥገኝነት ባገኙበት በአገራችን ለሚያገኙት ማንኛውም አገልግሎት ወጪው የሚሸፈነው ከአለም አቀፉ ማህበረሰብ በሚገኝ ብድርና እርዳታ ስለሆነ በአገራችን ላይ ምንም አይነት የበጀት ጫና አይኖረውም ያሉት አቶ ዘይኑ ጀማል ለስደተኞች ተብሎ በሚፈጠረው የስራ እድልም የአገራችን ወጣቶች ተጠቃሚ እንደሚሆኑና ስደተኞቹም በሚያገኙት አገልግሎት እንደማንኛው የአገሪቱ ዜጋ ታክስ እንደሚከፍሉ አስታውቀዋል፡፡

ስደተኛን አለመቀበል ከአለም አቀፍ ስምምነቱ አኳያ አስቸጋሪ ከመሆኑም ባሻገር ገጽታም ስሚያበላሽ ስደተኞችን ተቀብለን በእርዳታ ብቻ ከምናስቀምጥና የተፈጥሮ ሃብታችንን ከምንጎዳ በልማቱም እንዲሳተፉ ብናደርጋቸው ለአገራችን የሚኖረው ጠቀሜታ የጎላ ነው ብለዋል አቶ ዘይኑ ፡፡

የውይይቱ ተሳታፊዎች በበኩላቸው አዋጁ ቀደም ሲል የነበረ ቢሆንም የተሟላ ባለመሆኑ የአገራችንንና የዜጎቻችንን መብትና ጥቅም በማይጎዳ መልኩ እዲሻሻል መደረጉን በጥንካሬ አንስተው አሁንም ህጉ ከመጽደቁ በፊት መታየት ያለባቸው ነገሮች በጥልቀት እንዲታዩና ስደተኞችን መቀበል ከጀመርንበት ጊዜ አንስቶ እስከአሁን ድረስ የደረሰብንን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጫና ሊፈታ የሚችል ህግ ሊሆን ይገባል ሲሉ አሳስበዋል፡፡