ምክር ቤቱ ሁለት የብድር ስምምነቶችን አጸደቀ
ምክር ቤቱ ሁለት የብድር ስምምነቶችን አጸደቀ
(ዜና ፓርላማ) ግንቦት 26፣ 2017 ዓ.ም.፤ አዲስ አበባ፤ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ባካሄደው 33ኛ መደበኛ ስብሰባው ሁለት የብድር ስምምነቶችን አጽድቋል፡፡
የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር የተከበሩ ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር) በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ እና በአረብ ባንክ ለአፍሪካ ኢኮኖሚ ልማት መካከል ለተቀናጀ የውጤታማ ግብርና ኢንዱስትሪ ፓርክ ልማት ለወጣቶች ስራ እድል ፈጠራ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የተደረገውን የብድር ስምምነት ለማጽደቅ የቀረበ ረቂቅ አዋጅን በተመለከተ ማብራሪያ አቅርበዋል፡፡
በማብራሪያቸውም፣ ብድር ስምምነቱ በግብርና ኢንዱስትሪ ፓርኮችን ለማስፋፋት፣ የባለሙያዎችን አቅም ለመገንባት፣ የመስኖ አውታሮችና እና የግብርና ምርታማነትን ለማሳደግ እንዲሁም ወጣቶች በግብርና ኢንዱስትሪው ዘርፍ ተሳታፊ እንዲሆኑ የሚያስችል ስምምነት መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
በተጨማሪም የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትሩ በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ እና በዓለም አቀፍ የልማት ማህበር መካከል ለሴቶች እና ልጃ-ገረዶች ጤና የተቀናጀ ፣ ጠንካራ እና በፈጠራ እና በቴክኖሎጂ የታገዘ አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የቀረበውን የብድር ስምምነት ለማጽደቅ የቀረበ ረቂቅ አዋጅን አስመልከቶ ገለጻ አቅርበዋል፡
ስምምነቱ በጤናው አገልግሎት ዘርፍ ጥራት እና ተደራሽነትን ለማስፋት፣ በሴቶች ቅድመ-ወሊድ ላይ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ ችግሮችን ለመፍታት፣ የአየር ንብረት ለውጥን የሚቋቋሙ ምቹ የጤና ተቋማትን ለመገንባት እና የጤናውን ዘርፍ ተደራሽ ለማድረግ ያለመ ስምምነት መሆኑን አቅርበዋል፡፡
በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ እና በአረብ ባንክ ለአፍሪካ ኢኮኖሚ ልማት መካከል ለተቀናጀ የውጤታማ ግብርና ኢንዱስትሪ ፓርክ ልማት ለወጣቶች ስራ እድል ፈጠራ ፕሮጀክት ማስፈጸሚያ የተደረገውን የብድር ስምምነት ለማጽደቅ በቀረበ ረቂቅ አዋጅ አሳታፊነትን እና ተጠቃሚነትን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለተነሱ ጉዳዮች የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታው እዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ምላሽ አቅርበዋል፡፡
ፕሮጀክቱ ግብርና ላይ ያተኮሩ የኢንዱስትሪ ፓርኮችን ለማልማት ትልቅ ፋይዳ እንዳለው አብራርተው፣ የተገኘውን የልማት ሀብት በአግባቡ አሳታፊነቱ እና ተጠቃሚነቱ ተጠብቆ ስራ ላይ እንደሚውል ክትትል እና ቁጥጥር ይደረግበታል ብለዋል፡፡
ምክር ቤቱም የብድር ስምምነት ረቂቅ አዋጆቹን አዋጅ አድርጎ በሙሉ ድምጽ አጽድቋል፡፡
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives