ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው 25ኛ መደበኛ ስብሰባው ሁለት አዋጆችን አፀደቀ
------------------------
(ዜና ፓርላማ) ሚያዝያ 9 ቀን፣ 2017 ዓ.ም፤ 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ4ኛ ዓመት የስራ ዘመን 25ኛ መደበኛ ስብሰባው ሁለት ረቂቅ አዋጆች ላይ ተወያይቶ አፅድቋል።
ምክር ቤቱ በ25ኛ መደበኛ ስብሰባው ካፀደቃቸው አዋጆች መካከል የመገናኛ ብዙሃን አዋጅን ለማሻሻል የቀረበ ረቂቅ አዋጅ የመጀመሪያው ሲሆን ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ የዲሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ እውነቱ አለነ ሪፖርትና የውሳኔ ሀሳብ አቅርበዋል።
ምክር ቤቱም በቀረበው ረቂቅ አዋጅ ላይ በስፋት ከተወያየ በኋላ የመገናኛ ብዙሃንን አዋጅ ለማሻሻል የቀረበውን አዋጅ፤ አዋጅ ቁጥር 1374/2017 አድርጎ በ1 ተቃውሞ በአብላጫ ድምፅ አፅድቋል።
በመቀጠልም የተቀናጀ የውሃ ሀብት አስተዳደር ማስፈጸሚያ የተፋሰሶች ከፍተኛ ምክር ቤት ማቋቋሚያ ረቂቅ አዋጅን አስመልክቶ የውሃ፣ መስኖና ቆላማ አካባቢዎች እና አካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ ወ/ሮ ፈቲያ አህመድ ሪፖርትና የውሳኔ ሀሳብ አቅርበዋል።
ምክር ቤቱም የቀረበው ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ በስፋት ከተወያየ በኋላ የተቀናጀ የውሃ ሀብት አስተዳደር ማስፈጸሚያ የተፋሰሶች ከፍተኛ ምክር ቤት ማቋቋሚያ አዋጅን አዋጅ ቁጥር 1375/2017 አድርጎ በሙሉ ድምጽ በማፅደቅ ጉባኤውን አጠናቋል።
 
(በ ኃይለሚካኤል አረጋኸኝ)