ምክር ቤቱ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ረቂቅ አዋጅ መርምሮ አፀደቀ
ምክር ቤቱ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ረቂቅ አዋጅ መርምሮ አፀደቀ
(ዜና ፓርላማ) ግንቦት 26 ቀን፣ 2017 ዓ.ም፤ አዲስ አበባ፤ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ33ኛ መደበኛ ስብሰባው፤ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ረቂቅ አዋጅን መርምሮ በሙሉ ደምጽ አፅድቋል፡፡
የውሃ፣ መስኖ፣ ቆላማ አካባቢና አካባቢ ልማት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ የተከበሩ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር )ሪፖርት እና የውሳኔ ሃሳብ ለምክር ቤቱ አቅርበዋል፡፡
እንደ ሀገር የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ረቂቅ አዋጅ ማፅደቁ፤ በአካባቢና በሰዎች ደህንነትና ጤና ላይ እየደረሰ ያለውን ጉዳት ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚያስችል መሆኑን የተከበሩ አወቀ አምዛዬ (ዶ/ር )አስረድተዋል፡፡
በክልሎች እና ከተማ አስተዳደሮች አስፈላጊ መሠረተ ልማቶችን ያሟላ የደረቅ ቆሻሻ ሥርዓት ለመዘርጋት ኃላፊነትና ግዴታዎችን ለመደንገግ ረቂቅ አዋጁ የሚያግዝ መሆኑ የተከበሩ አወቀ (ዶ/ር) አያይዘው ገልጸዋል፡፡
ቅጣቱ አንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ ሊውሉ በሚችሉ ስስ የፕላስቲክ ምርቶች ላይ ታሳቢ ያደረገ መሆኑን የተከበሩ አወቀ (ዶ/ር) ገልጸው፤ ክልሎች እና የከተማ አስተዳደሮች የአካባቢን ነበራዊ ሁኔታ ታሳቢ በማድረግ የውስጥ ደንብና መመሪያ አውጥተው መተግበር እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡
ከደረቅ ቆሻሻ አያያዝ፣ አወጋገድ እና አስተዳደር ጋር በተያያዘ በቀጣይነት በዘመቻ መልክ ህብረተሰቡ ኃላፊነቱን እና ግዴታውንም ጭምር እንዲወጣ የግንዛቤ ስራ በስፋት እንደሚሰራ የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ አስረድተዋል፡፡
ረቂቅ አዋጁ ለሀገር እና ለአካባቢ ንፅህና ያለው ጠቃሜታ እንዳለ ሆኖ የቅጣቱ መጠን የህብረተሰቡን የኢኮኖሚ አቅም ታሳቢ ያደረገ መሆኑ እንዳለበት የምክር ቤት አባላት አስገንዝበዋል፡፡
የምክር ቤት አባላት ረቂቅ አዋጁ የአካባቢ ሥነ-ምህዳርን ለመጠበቅ ጠቀሜታው የጎላ መሆኑን ገልጸው፤ ችግሩን ከምንጩ ለማድረቅ ለፕላስቲክ አምራች እና አቅራቢ ደርጅቶች ላይ የግንዛቤ ስራ መስራት እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡
በቀጣይ ከረቂቅ አዋጁ ትግበራ ጋር በተያያዘ ህዝቦች በግንዛቤ እጥረት ለቅጣት ተጋላጭ እንዳይሆኑ በስፋት የግንዛቤ ስራ መሰራት እንዳለበት የምክር ቤት አባላት አክለው አሳስበዋል፡፡
ምክር ቤቱ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ረቂቅ አዋጅ፤ አዋጅ ቁጥር 1383/2017 አድርጎ በሙሉ ድምጽ አፅድቋል፡፡
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives