የመንግሥትና ሕዝብ ሀብትን ለታለመለት ዓላማ ለማዋል መሥራት ይገባል
የመንግሥትና ሕዝብ ሀብትን ለታለመለት ዓላማ ለማዋል መሥራት ይገባል
(ዜና ፓርላማ) ግንቦት 27፣ 2017 ዓ.ም፤ የመንግሥትንና ሕዝብ ሀብት ከብልሹ አሠራር ተጠብቆ ለታለመለት ዓላማ እንዲውል መሥራት ያስፈልጋል አሉ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈጉባዔ ሎሚ በዶ።
23ኛው የፌዴራል፣ የክልልና የፌዴራል ከተማ አሥተዳደሮች ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤቶች እንዲሁም የባለድርሻ አካላት ዓመታዊ መደበኛ ጉባዔ በአርባ ምንጭ ከተማ እየተካሄደ ነው፡፡
ምክትል አፈ ጉባዔ ሎሚ በጉባዔው ላይ ባደረጉት ንግግር፤ የተቋማት ብልሹ አሠራር በመንግሥት ላይ ያለው አመኔታ እንዲሸረሸርና የሕዝብ እርካታ በመቀነስ የሕዝብ ቅሬታ እንዲጨምር ያደርጋል ብለዋል።
በመሆኑም በየደረጃው የሚገኙ ተቋማት ከሙስናና ብልሹ አሠራር በመራቅ ኃላፊነትን በአግባቡ በመወጣት የሀገርን የልማት ፍላጎት ማሟላት የሚችል የፋይናንስ አሠራር ሊከተሉ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡
በተቋማት ዘንድ ግልጽነትና ተጠያቂነት እንዲኖር እንዲሁም ለብልሹ አሠራር ምንጭ የሆኑ አካላት ላይ ሕጋዊ ርምጃ እንዲወሰድ የአሠራር ነፃነታቸው የተጠበቀ የኦዲት መሥሪያ ቤቶች ሊኖሩ እንደሚገባም አስረድተዋል፡፡
የፌደራል ዋና ኦዲተር መሠረት ዳምጤ በበኩላቸው፤ የሀገርን ሀብት ከብልሹ አሠራርና ብክነት ለመታደግ ከፌዴራል እስከ ክልል ባሉ ኦዲተር መሥሪያ ቤቶች ወጥ የሆነ አሠራር ተዘርግቶ እየተሠራ መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
የኦዲት ሥራ ወጥ የሆነና ዓለም አቀፋዊ እንዲሆን፤ የተለያዩ ሀገራት ልምዶችን በመቅሰም ከሀገራዊ ነባራዊ ሁኔታዎች ጋር ተጣጥመው እንዲተገበሩ እየተሠራ እንደሚገኝም ተናግረዋል፡፡
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives