የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ

የተከበሩ አቶ ታገሠ ጫፎ  መልዕክት

በዴሞክራሲ ማሕበረሰብ ፓርላማ የፖለቲካ ተሳትፎ መገላጫ ነው፡፡ የፓርላማ ዴሞክራሲ ሥርዓት በአንድ አገር መጠናከር ለዜጎች የዴሞክራሲ ተሳትፎ መጎልበት፣ ለሕግ የበላይነትና ለማህበራዊ ፍትሕ መረጋገጥ ወሳኝ ሲሆን አስፈፃሚው  የመንግሥት አካል በተጠያቂነትና በግልፅነት ስራውን እንዲያከናወን ያስችላል፡፡

በሀገራችን የፓርላማ ዴሞክራሲ ስርዓት መተግበር ከጀመረ ሦስት አስርት ዓመታት  የተቆጠሩ ሲሆን አምስት የምክር ቤት ዘመናት አልፈው እነሆ አሁን በ6ኛው ምክር ቤት 4ኛ  ዓመት  የሥራ ዘመን ላይ እንገኛለን፡፡

የኢፌዲሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፌደራሉ መንግሥት ከፍተኛ የሥልጣን አካል ነው፡፡ በየአምስት ዓመቱ በሚካሄድ ብሔራዊ ምርጫ የሕዝብ ይሁንታ አግኝተው በሚመረጡ አባላት ይመሰረታል፡፡ አባላቱም ሁሉ አቀፍ፣ ነፃ፣ ቀጥተኛ፣ ትክክለኛ በሆነና ድምጽ በሚስጥር በሚሰጥበት ሥርዓት በሕዝብ ይመረጣሉ፡፡አባላቱ ተጠሪነታቸው ለኢትዮጵያ ሕዝብ ነው፤ ተገዥነታቸውም ለሕገ መንግሥቱ፣ ለሕዝቡና ለሕሊናቸው ነው፡፡

ምክር ቤቱ በሕግ አወጣጥ፣ በክትትልና ቁጥጥር እንዲሁም በውክልና ሥራዎች የሚያከናውናቸው ተግባራት እና የሚያስተላልፋቸው ውሳኔዎች ወሳኝ መሆናቸው ይታወቃል፤ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በእያንዳንዱ ዜጋ  ሕይወት  ላይ  በአወንታዊም ሆነ በአሉታዊ ተፅዕኖ ማሳደራቸው ግልፅ ነው፡፡

በመሆኑም ምክር ቤቱ ለሀገር ሠላም፣ ለዜጎች ማህበራዊ ልማትና ሁለንተናዊ ብልፅግና መረጋገጥ አስፈላጊ ናቸው ተብለው በታመኑ ጉዳዮች ላይ በሕግ አወጣጥ ሂደት፣ በክትትልና ቁጥጥር እና በውክልና ተግባራት ተገቢውን ምርመራ በማካሂድ በርካታ ሀገራዊ ውሳኔዎችን ሲያሳልፍ ቆይቷል፡፡ ለሀገራዊ እቅዶች፣ፕሮግራሞች፣ፖሊሲዎችና ፕሮጀክቶች መፈፀም ፤ የመንግሥትና ሕዝብ ሃብትና ንብረት ለታለመለት ዓላማ ውለው የሕዝብ የኑሮ ደረጃ እንዲሻሻል የመንግሥት ተቋማት ተልዕኳቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ምክር ቤቱ ጠንከራ የክትትልና ቁጥጥር ስራ ሰርቷል፤ እየሰራም ይገኛል፡፡

ህብረተሰቡ የሚያነሳቸው የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች ምላሽ እንዲያገኙ ምክር ቤቱ ከመቼውም ጊዜ በላይ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ሲሆን የተቋማት ምላሽም እያደገና እየተሻሻለ መጥቷል ማለት ይቻላል፡፡

በፓርላማ ዲፕሎማሲው ዘርፍ የሀገራችንን ባሕልና እውነተኛ ገፅታ ለማስተዋወቅና የሀገሪቱን የኢኮኖሚ ዲፕሎማሲ (ንግድና ኢንቨስትመንት) ከመደገፍ ረገድ አበረታች ውጤቶች ለማስመዝገብ የሁለትዮሽና በብዙኽዮሽ መድረኮችን በአግባቡ ለመጠቀም ጥረት ተደርጓል፤ በቀጣይም የፓርላማ ዲፕሎማሲን እንደ አንድ የውጭ ፖሊሲ መሳሪያ በስፋትና በተጠናከረ አግባብ ተግባራዊ ለማድረግ  ምክር ቤቱ በትኩረት የሚሰራ ይሆናል፡፡

የዜጎችን የኑሮ ደረጃ ለማሻሻል የተጓተቱ ፕሮጀክቶች ፈጥነው ተጠናቀው ለህብረተሰቡ የልማት አገልግሎት እንዲሰጡ፣ኢንቨስትመንት እንዲስፋፋ፣በሥራ ፈጠራና ድህነት ቅነሳ፣ ለሕግ የበላይነትና ለመልካም አስተዳደር መረጋገጥ ምክር ቤቱ በቀጣይ ጊዜያት  በትኩረት የሚሰራ ይሆናል፡፡  

ያሉብንን የፖለቲካ ልዩነቶች በንግግር፣ በምክክርና በውይይት ለመፍታት ምክር ቤቱ የአቋቋመው ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን በአሁኑ ወቅት በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች በአጀንዳ ማሰባሰብ ሂደት ላይ ይገኛል፡፡ ለኮሚሽኑ ተልዕኮ መሳካት ሁላችንም ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን በሀገራዊ የፍቅር ስሜት የበኩላችን ድርሻ ልንወጣ ይገባል፡፡

የአንድነታችን ተምሳሌትና የአብሮነታችን ማሳያ የሆነው ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድባችን በመጠናቀቅ ሂደት ላይ የሚገኝ ሲሆን የዜጎችን ማህበራዊ ኢኮኖሚ ልማት የሚያፋጥኑ በርካታ ትላልቅ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች እየተከናወኑ ይገኛሉ፡፡

ሥለሆነም ሀገራችን የጀመረችውን ሁለንተናዊ ብልፅግና ጉዞ ከዳር ለማድረስና ለዜጎቿ ምቹ የሆነች ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ ኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ለሠላም፣ ለአብሮነታችን መጎልበትና ለብሔራዊ መግባባት አብረን እንድንቆምና ሁላችንም የየራሳችንን አበርክቶ እንድንወጣ በዚህ አጋጣሚ መልዕክት አስተላልፋለሁ፡፡ አዲሱ ዓመት የሠላም፣ የደስታ፣ የአብሮነት፣ የመግባባት፣ የልማት እና ብዙ ተስፋዎች የምናይበት ዘመን እንዲሆን ልባዊ ምኞቴ ነው፡፡

                                                          አመሠግናለሁ!