የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት አፈ ጉባኤ የተከበሩ አቶ ታገሠ ጫፎ የአሜሪካ ሴናተርን በጽ/ቤታቸው ተቀብለው አነጋገሩ

አፈ ጉባኤ የተከበሩ አቶ ታገሠ ጫፎ የአሜሪካ ሴናተር አባል  ከሆኑት ጀምስ ኢንሆፎ  ጋር በቀጠናዊና ሃገራዊ ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርገዋል፡፡

በውይይቱ የተከበሩ አፈ ጉባኤ አቶ ታገሰ  በህዳሴ ግድብ ፣ በህግ ማስከበር፣ በሰብአዊ እርዳታ ተደራሽነት ፣ ከሱዳን ድንበር ማስከበር ሥራ ጋር ተያይዞ ያለበትን ደረጃ እና እየተከናወኑ ያሉትን ተግባራት  ላይ ማብራሪያ ሰተዋል፡፡ 

በማብራሪያቸው ኢትዮጵያ ሁለተኛውን ዙር የህዳሴ ግድብ የሙሌት ሥራ ለማከናወን በዝግጅት ላይ መሆኗን ገልፀው፣ የተፋሰሱን ሃገራት ጥቅም በማይነካ መልኩ እንደሚፈፀም ገልፀዋል፡፡

ከህግ ማስከበር ጋር ተያይዞ የተከሰቱ ችግሮችን ደረጃ በደረጃ ለመፍታት እየተሠራ መሆኑን የገለፁት አፈ ጉባዔ የሰብዓዊ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖችም ድጋፍ በመደረግ ላይ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ኢትዮጵያ ከሱዳን ድንበር ጋር ተያይዞ በየጊዜው የሚነሱ ግጭቶችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት ዝግጁ መሆኗንም በዚሁ ጊዜ ተናግረዋል፡፡

ሴናተር ጀምስ ኢንሆፍ በተደረገላቸው አቀባበል ደስተኛ መሆናቸውን ገልፀው የተሰጠው ማብራሪያ በኢትዮጵያ እየተደረገ ያለውን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ  ለመረዳት እንዳስቻላቸው ገልፀዋል፡፡

አክለውም ኢትዮጵያ በምታከናውናቸው ተግባራት ሁሉ ድጋፍ ለማድረግ ቁርጠኛ መሆናቸውን ሴናተር ጀምስ አረጋግጠዋል፡፡