"ረቂቅ አዋጁ ለአገር ኢኮኖሚ እድገትና የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ሚናው የጎላ ነው"

(ዜና ፓርላማ) ሰኔ 12 ፣ 2017 ዓ.ም.፤ ረቂቅ አዋጁ ለሀገር ኢኮኖሚ እድገትና የዜጎችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ሚናው የጎላ መሆኑን በኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የከተማ መሠረተ ልማት እና የትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ገለፀ።

ቋሚ ኮሚቴው የውጭ አገር ዜጎች በኢትዮጵያ የማይንቀሳቀስ ንብረት ባለቤት ወይም ባለይዞታ የሚሆኑበትን አግባብ ለመደገፍ በተዘጋጀ ረቂቅ አዋጅ ላይ ከተለያዩ ተቋማት ኃላፊዎች ጋር ውይይት አድርጓል።

ከዚህ ቀደም በረቂቅ አዋጁ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት መደረጉ የሚታወቅ ሲሆን በትላንትናው እለትም ከተለያዩ ተቋማት ከመጡ ኃላፊዎች ጋር በረቂቅ አዋጁ ተገቢነት ላይ እንዲሁም መታየት አለባቸው በተባሉ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት ተካሂዷል።

በውይይቱ ላይ ከተገኙ ተቋማት መካከልም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ የፌደራል ጠበቆች ማህበር፣ የኢሚግሬሽንና ዜግነት አገልግሎት እና የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ይገኙበታል።

የውይይቱ ተሳታፊዎችም በረቂቅ አዋጁ ዙሪያ በርካታ ጥያቄዎችንና አስተያየቶችን አንስተዋል።

ከተነሱት መካከልም የቤት (የመሬት) ባለቤትነት ከህገመንግስቱ አኳያ ለዜጎች የተሰጠ መብት በመሆኑ ረቂቅ አዋጁ ከህገመንግስቱ ድንጋጌ ጋር አይጣረስም ወይ? ለዜጎች የስራ ዕድል ከመፍጠር አኳያ መልካም ገፅታ እንዳለው የተጠቀሰ ቢሆንም ነገር ግን የውጭ ዜጎች የማይንቀሳቀሱ ንብረቶችን ገዝቶ በመሸጥ ሂደት ውስጥ ምን አይነት የስራ እድል ይፈጥራል እና ሌሎችም ከህግ እና ከኢኮኖሚያዊ ፋይዳ አንፃር የቀረቡ ጥያቄዎች በዋነኛነት ተጠቃሽ ናቸው።

የከተማ መሰረተ ልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ  ሰብሳቢ የተከበሩ መሀመድ አብዶ (ፕ/ር) ከሚመለከታቸው ተቋማት የተነሱት ሁሉም ጥያቄዎችና አስተያየቶች አግባብነት ያላቸው መሆኑና ረቂቅ አዋጁን ይበልጥ ለማዳበር የሚያግዙና በግብዓትነት የሚወሰዱ መሆናቸውን ገልጸዋል።

የማይንቀሳቀስ ንብረት ከሚለው አገላለጽ አኳያ የተለያዩ ጥያቄዎች የሚያስነሳ ነው ያሉት ሰብሳቢው ብዥታን ለማጥራት ከምን አንፃር እንደተገለፀ አቅጣጫ መስጠት ወይም በቀጥታ የመኖሪያ ቤት በሚለው መተካት ያስፈልጋል ሲሉ አሳስበዋል።

የቋሚ ኮሚቴ ም/ሰብሳቢ የተከበሩ እሸቱ ተመስገን (ዶ/ር) በበኩላቸው የቀረበው ረቂቅ አዋጅ ከህገመንግስታችን እና ከኢንቨስትመንት አዋጅ ጋር ምንም አይነት መጣስና ተቃርኖ እንደሌለበት አጥርቶ ማስቀመጥ እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።

የውጭ ዜጎች የሚለውን አባባል በተመለከተ ለህዝብ ግልጽነትን ከመፍጠር አኳያ ትውልደ ኢትዮጵያንን የሚመለከት መሆኑን በረቂቅ አዋጁ በግልጽ ማመላከት እንደሚገባም አሳስበዋል።

የተከበሩ እሸቱ (ዶ/ር) አያይዘውም አዋጁ ሲፀድቅ ምንም እንኳን የከተማ መሰረተ ልማት ሚኒስቴር በኃላፊነት የሚሰራ ቢሆንም ተቋሙ ሌሎች ቁልፍ ስራዎችን የሚሰራ በመሆኑ የአዋጁን ተፈጻሚነት ለማረጋገጥ የተለያዩ ኮሚቴዎችን በማዋቀር ማገዝ እንደሚገባ ተናግረዋል።

አዋጁ ከመፅደቁ በፊት እውነት ላይ በመመስረት ግልጽኝነትን ለመፍጠር እንዲሁም አዋጁ ለታለመለት ዓላማ እንዲውል ከማስቻል አንፃር ይህ ውይይት አስፈላጊ ነው ሲሉም ጠቁመዋል።

የከተማ መሰረተ ልማት ሚኒስትር ዴኤታ ሄለን ደበበ ረቂቅ አዋጁ ለማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያ ትልቅ ጠቀሜታ እንዳለው አንስተው፤ የአዋጁን አስፈላጊነት በሚገባ ለማስጨበጥ ጥረት መደረጉን አብራርተዋል።

ትልልቅ ካፒታል ያላቸው ሀገራት ሀውሲንግ ዘርፋ ላይ ኢንቨስት የማድረግ ፍላጎት እንዳላቸው በተለያየ መንገዶች ይገልፃሉ ያሉት ሚንስትር ዴኤታዋ የህግ ማዕቀፎቻችንን ምን ፈቃጅ እና ከልካይ ሁኔታዎች እንዳሉ የሚጠይቁ በመሆኑ ይህ ረቂቅ አዋጅ መልስ የሚሰጥና ለኢንቨስትመንትም በር ከፋች ነው ሲሉ ጠቁመዋል።

በመሆኑም ለዘርፉ ቀጥተኛ በሆነም፤ ቀጥተኛ ባልሆነም መልኩ ብዙ ዕድሎችን የሚፈጠር መሆኑንም ገልጸዋል።

(በቃልኪዳን ተሰማ)