" ከሕዝብ የሚነሱ ጥያቄዎችን ዘላቂነት ባለው መልኩ ምላሽ ለመስጠት ተቋማት ትኩረት ሰጥተው ሊሰሩ ይገባል " ምክትል አፈ ጉባዔ
" ከሕዝብ የሚነሱ ጥያቄዎችን ዘላቂነት ባለው መልኩ ምላሽ ለመስጠት ተቋማት ትኩረት ሰጥተው ሊሰሩ ይገባል " ምክትል አፈ ጉባዔ
(ዜና ፓርላማ) ግንቦት 13 ፣ 2017 ዓ.ም፤ ከሕዝብ የሚነሱ ጥያቄዎችን ዘላቂነት ባለው መልኩ ምላሽ ለመስጠት የአስፈፃሚ ተቋማት ትኩረት ሰጥተው ሊሰሩ እንደሚገባ የኢፌዴሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ ጉባዔ የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ በዶ ተናግረዋል።
የምክር ቤቱ አባላት ከመረጣችው ሕዝብ ጋር በየካቲት ወር ባደረጉት ውይይት ለተነሱ ጥያቄዎች የተሰጡ ምላሾች እየተገመገሙ ነው።
ዘንድሮ ለሰባተኛ ጊዜ በተከናወነው የሕዝብ ውክልና ሥራ በየካቲት ወር የምክር ቤት አባላት ወደ ተመረጡበት አካባቢ በመሄድ ከኅብረተሰቡ ጋር ሰፊ ውይይት አድርገዋል፡፡
ከሕዝብ የተነሱ ጥያቄዎች በምክር ቤቱ ተገምግመው ለሚመለከታቸው ሚንስቴር መ/ቤቶች እና ተጠሪ ተቋማት በተላከው መሠረት ምላሽ የተሰጣቸውን ለመገምገም ሚንስትሮች በምክር ቤቱ በተገኙበት ውይይት እየተደረገ ነው።
ካሉት 482 የምርጫ ክልሎች በ312 የህዝብ ውክልና ሥራ የተሰራ ሲሆን አፈፃፀሙም 65 በመቶ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
ከየምርጫ ክልሉ ከመራጩ ህዝብ የተሰበሰቡ ጥያቄዎች በየደረጃው ላሉ የክልልና የፌዴራል ተቋማት የተላኩ ሲሆን በፌዴራል ደረጃ ለ50 ሚንስቴር መ/ቤቶች እና ለተጠሪ ተቋማት መላኩን የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ ገልፀዋል።
በሕገ-መንግሥቱ ለምክር ቤቱ ከተሰጡት አራት ዋና ዋና ተግባራት መካከል ዋናና መሠረታዊ የሆነውን የሕዝብ ውክልና ሥራ መሆኑን የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ ገልፀዋል።
የምክር ቤቱ አባላት በአመት ሁለት ጊዜ ከመረጣቸው ሕዝብ የሚነሱ የልማት እና የማደግ ጥያቄዎችን መሠረት ባደረጉና በሌሎቾም ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት እንደሚደረግ የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ ተናግረዋል።
በሕዝብ ውክልና ሥራ በምክር ቤቱ የወጡ ሕጎችን ተፈፃሚነት እና በአስፈፃሚ ተቋማት በኩል የወጡ ስትራቴጂዎች ፣ ዕቅዶች፣ ኘሮግራሞች እንዲሁም የተለያዩ አሠራሮችን መሠረት ያደረጉ ተግባራት በምን ደረጃ እየተፈፀሙ እንደሆነ የማረጋገጥ ሥራም እንደሚሰራ ነው ያሉት ምክትል አፈ ጉባዔዋ።
ከሕዝቡ የሚነሱ ጥያቄዎችን መሠረት በማድረግ ችግሮች በወቅቱ ምላሽ እንዲያገኙ እና ኃላፊነታቸውን በአግባቡ የማይወጡ የሥራ ኃላፊዎችን ተጠያቂ እንዲሆኑ ለማድረግ እንደሚሰራም ምክትል አፈ ጉባዔ አብራርተዋል።
ለሕዝብ ጥያቄ ተገቢውንና ወቅቱን የጠበቀ ምላሽ በመስጠት የሕዝቡንና የሀገርን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚገባም ተናግረዋል።
በሕዝብ ውክልና ሥራዎች እንደ ሀገር እየተከናወኑ ባሉ ሁሉን አቀፍ ተግባራት የሕዝቡን ተሣታፊነትና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችሉ ሥራዎች መሰራት እንዳላባቸው ተናግረዋል።
በሠላምና ፀጥታ፣ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ፣ የአገልግሎት አሰጣጥ፣ የመልካም አስተዳደር ችግሮች፣ የመሠረተ ልማት ዝርጋታዎች፣ በፌዴራል መንግስት የሚሰሩ ፕሮጀክቶች እንዲሁም ተጨማሪ የመልማትና የማደግ ፍላጎቶች በሕዝቡ ከሚነሱ ጥያቄዎች ዋና ዋናዎቹ ናቸው።
Copyright 2020 - All rights reserved. House of Peoples' Representatives