null Eritrean refugees should get appropriate support: House

በትግራይ ክልል ለሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች የሚደረገው ድጋፍ ውስንነት እንዳለበት ተገለጸ፣

በትግራይ ክልል ለሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች የሚደረገው ድጋፍ ውስንነት እንዳለበት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አስታወቀ፡፡

የቋሚ ኮሚቴው አባላት ሰሞኑን  በትግራይ ክልል  በተለያዩ ወረዳዎች  በእንዳባ ጉና፣ በማዕይኒ፣ በዓዲ ሓሩሽ እና በህፀፅ እንዲሁም በሽመልባ ካንፖች የሚገኙትን የኤርትራውያን ስደተደተኞች መጠለያ ተዘዋውረው በጎበኙበት ወቅት ለስደተኞች የመጠለያ፣ የምግብ፣ የውሀ አቅርቦት፣ የመፀዳጃና የህክምና አገልሎት አሰጣጥ ውስንነት እንዳለበት አረጋግጠዋል፡፡

አለም አቀፍ ግብረ-ሰናይ ድርጅቶች በካምፕ ለሚኖሩ ኤርትራውያን ስደተኞች በሚያደርጉት የትምህርት እና የህክምና ድጋፍ የአካባቢውን ነዋሪ ህዝብ ጨምሮ ተጠቃሚ ከማድረግ አንጻር ክፍተት እንዳላባቸው የቋሚ ኮሚቴው አባላት መረዳት ችለዋል፡፡

በሌላ በኩል ስደተኞች ከነዋሪው ማህበረሰብ ጋር ያላቸው ማህበራዊ ግንኙነት እንዲጠናከር በአዝመራ ስብሳቦ፣ በአፈርና ውሀ ጥበቃ ስራዎች እየተሳተፉ ሲሆን ደህንነታቸውን ለመጠበቅ የክልሉ ጸጥታው ዘርፍ በትኩረት እየሰራ መሆኑን ነው የቋሚ ኮሚቴው አባላት የተገነዘቡት፡፡

የካምፕ አስተባባሪዎች እንደገለጹት የትግራይ ክልላዊ መንግስትና ህዝብ ከድንበር ጀምሮ  ለስደተኞች የምግብ፣ የትራንስፖርት፤የህክምና አገልግሎት በመስጠት የበኩላቸውን አስተዋፆ ያበረከቱ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የእንዳባ ጉና የስደተኞች ማጣሪያ ጣቢያ አስተባባሪ አቶ ሀዱሽ ኪዳኑ እንዳሉት ወደ ትግራይ ክልል የሚገቡት የኤርትራውያን ስደተኞች ቁጥር በአማካኝ ሲሰላ በቀን ከ300 እስከ 400 የሚደርስ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በሁለቱ አገራት መካከል የሰላም ስምምነት ከተደረገ ወዲህ የስደተኞች አሃዝ እየጨመረ በመምጣቱ ምክንያት በነዋሪው ማህበረሰብ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ከማሳደሩም ባሻገር የበጀት እና የሰው ሀይል እጥረት የተከሰተ መሆኑን ነው አቶ ሀዱሽ የገለጹት፡፡

ስደተኞች እንዳሉት የኤርትራ እና የትግራይ ህዝቦች በደም፣ በባህልና በቋንቋ የተጋመዱ የሁለት አገር ወንድማማች ህዝቦች መሆናቸውን ገልጸው የትግራይ ክልላዊ መንግስትና ህዝብ ከድንበር ጀምሮ እስከ መጠለያ ካምፕ ድረስ ላደረጉላቸው መልካም አቀባበል ምስጋና አቅርበዋል፡፡

በሌላ በኩል የመጠለያ፣ የአልባሳት፣ የምግብና የውሃ አቅርቦት፣ እንዲሁም የመጸዳጃ ቤት፣ እና የህክምና አገልግሎት ችግሮች እንዳሉባቸው የገለጹ ሲሆን ስደተኛ ህፃናት ካዋቂዎች የተለየ የምግብ አቅርቦትም ሆነ እንክብካቤ የማይደረግ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ባላፉት አመታት ለስደተኛ ተማሪዎች ይፈቀድ የነበረው የዩኒቨርስቲ ትምህርት እድል አሁን ላይ በመቋረጡ መክንያት ተምረው እራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን መርዳት የሚችሉ ወጣቶች ስራ ፈተው መቀመጣቸውን ተናግረዋል፡፡  

የአካባቢው ማህበረሰብ አባላት እንዳሉት የኤርትራውያን ስደተኞች ወደ አካባቢያቸው ሲመጡ መንግስት  መሰረተ ልማቶችን አሟልቶ ሁሉንም ማህበረሰብ ተጠቃሚ ለማድረግ የገባውን ቃል ባለመጠበቁ ምክንያት የኑሮ ውድነት መባባስ እና የተፈጥሮ ሀብት መመናመን ችግር እየገጠማቸው መሆኑን ቅሬታቸውን ገልጸው መንግስት ለጉዳዩ ልዩ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

የኤርትራ ስደተኞች ማስተባበሪያ ፅ/ቤት ኃላፊ አቶ ተኪኤ ገብረ እየሱስ በበኩላቸው ከተመዘገቡ 240 ሺህ ኤርትራውያን ስደተኞች 60 ሺህ የሚሆኑት በመጠለያ ካምፖች እየኖሩ እንደሆነ ገልጸው ያሉባቸውን ችግሮችን ለመቅረፍ ጥረት እተደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አባልና የቡድኑ አስተባባሪ የተከበሩ አቶ ድርቡ ጀማል በሰጡት ግብረ መልስ ስደተኞች ከማህበረሰቡ ጋር ያላቸውን ማህበራዊ ግንኙነት፣ የቴል ተጠቃሚ እንዲሆኑ መደረጉን በስደተኞች አዋጅ ዙሪያ ግንዛቤ መፈጠሩን በጥንካራ ጎን አመላክተዋል፡፡

በአንጻሩ ለስደተኞች የሚደረገው ሁለንተናዊ ድጋፍ እየቀነሰ ከመምታጡ ጋር ተያይዞ በመጠለያ፣ በህክምና፣ በምግብ፣ በውሃ እና በአማራጭ የሀይል አቅርቦት ዙሪያ ስር የሰደዱ ችግርች መኖራቸውን ነው በክፍተት የጠቆሙት፡፡

በመጨረሻም በክልሉ መንግስትና ህዝብ፣ እንዲሁም በግብረ- ሰናይ ድርጅቶች አማካኝነት ለኤርትራውያን ስደተኞች የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ መቀጠል አለበት ያሉት አቶ ድርቡ፣ በማህበረሰብና በስደተኞች የሚነሱ ቅሬታዎችን ለመፍታት ጥረት መደረግ እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

ዘጋቢ:- ተስፋሁን ወልተንጉስ