null Federal Employment and Food Security Agency should reaffirm its debt and working shads used for job creations.

የፌደራል የከተሞች የስራ ዕድል ፈጠራና የምግብ ዋስትና ኤጀንሲ በስራ ፈጠራ፣ ለስራ ፈጠራ የዋሉ ብድሮችንና ከተቀመጠው የጊዜ ገደብ በላይ የቆዩ የማምረቻና መሸጫ ሼዶችን በማስመለስ ላይ በትኩረት መስራት እንዳለት ተገለፀ፡፡

ይህ የተጠቆመው የኢፌድሪ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የከተማ ልማትና ኮንስትራክሽን ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኤጀንሲው ባደረገው መስክ ምልከታ ወቅት ነው፡፡

ቋሚ ኮሚቴ ሚያዚያ 7 ቀን 2011 ዓ.ም. የኤጀንሲውን የስራ እንቅስቃሴ ቃኝቷል፤ በቁልፍ ተግባራት አፈጻፀምና ባጋጠሙ ችግሮች ዙሪያም የኤጀንሲውን የስራ ሀላፊዎችና ሰራተኞችን አወያይቷል፡፡

በውይይቱም የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ ዘነበ ኩሞ በስራ ዕድል ፈጠራ በኩል በ6 ወራት ውስጥ ያለው አፈጻጸም 80% መድረሱን በከተማ የምግብ ዋስትና በ11 ከተሞች ከ445 ሺህ በላይ ዜጎች በዘላቂ ድጋፍና በሴፍቲኔት ፕሮግራም በአካባቢ ልማት ላይ በመሳተፍ ተጠቃሚ መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡

አመላመላቸውም በህብረተሰቡ በቂ ግምገማ ተደረጎ መሆኑንም አመልክተዋል፡፡ የአለም ባንክ ሂደቱን በጥሩ አፈጻጸም የገመገመ በመሆኑ ስራው ተጠናክሮ እንደሚቀጥልም ነው ሀላፊው የተናገሩት፡፡

ይህ እንዳለ ሆኖ የፋይናንስ አቅቦት፣ የመስሪያ ቦታ፣ ብድር እና ሼዶችን በማስመለስ ሂደት ላይ የሚስተዋሉትን ችግሮች በእጥረት አንስተዋል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው አባላት በበኩላቸው በስራ ዕድል ፈጠራ ላይ እየታየ ያለው መቀዛቀዝ እና የማምረቻና የመሸጫ ሼዶችን በተቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ለምን ማስመለስ እንዳልተቻለ የጠየቁ ሲሆን፤ የስራ እድል ፈጠራው የተቀዛቀዘው በአገሪቱ አንዳንድ ቦታዎች በተከሰተው አለመረጋጋት ምክንያት መሆኑን፣ ለስራ ዕድል ፈጠራ ተጠቃሚዎች የሚሰጡ የማምረቻና የመሸጫ ሼዶች ለ5 አመታት ቢሆንም 10 እና ከዚያም በላይ አመታት ተጠቅመው ያልመለሱ አካላት መኖራቸው ተጠቁሞ በቀጣይ እነዚህን አካላት በመለየት የማስመለስ ስራ እንደሚሰራ ነው የኤጀንሲው የስራ ሃላፊዎቹ ምላሽ የሰጡት፡፡

የቋሚ ኮሚቴው አባላት የኤጀንሲውን የለውጥና የመልካም አስተዳደር፣ የሴቶችጉዳይ፣ የውስጥ ኦዲት፣ የሂሳብና የንብረት አስተዳደር ክፍሎችን የስራ እንቅስቃሴ ተዟዙረው ተመልክተዋል፡፡

የኤጀንውን ሰራተኞች ባወያዩበት ወቅትም በአገሪቱ አንዳንድ ቦታዎች ያለው አለመረጋጋት ስራቸውን ከቦታ ቦታ ተዘዋውረው ለመስራት ስጋት እንዳሳደረባቸው፣ የሚከፈላቸው የቀን አበልም የወቅቱን የኑሮ ደረጃ ያላገናዘበና የቢሮ አጥረትም ጭምር እንዳለባቸው ሰራተኞች ለቋሚ ኮሚቴ አባላት ተናግረዋል፡፡

በመጨረሻም የቋሚ ኮሚቴው ቡድን የመሩት የተከበሩ አቶ ታደሰ ሆርዶፋ የመስክ ምልከታውን አስመልክቶ ለኤጀንሲው የስራ ሃላፊዎች በሰጡት ግብረ መልስ ኤጀንሲው በስራ ዕድል ፈጠራና በከተሞች የምግብ ዋስትና ዙሪያ ያከናወናቸውን ተግባራት፣ የለውጥ ስራ ትኩረት ተሰጥቶት መሰራቱንና ፈጻሚዎችም መለየታቸውን፣ የመልካም አስተዳደርና የኪራይ ሰብሳቢነት ማክሰሚ ዕቅድ መዘጋጀቱን እንዲሁም የተጠናከረ የውስት ኦዲት መኖሩን ቋሚ ኮሚቴው በጠንካራ አፈጻጸም እንደተመለከተው ገልጸዋል፡፡

በሌላ በኩል ለስራ ዕድል ፈጠራ የተሰጡ ብድሮችንና የማምረቻና መሸጫ ሼዶችን በአግባቡ ያለማስመለስ፣ በቢሮ ጥበት ሳቢያ ምቹ የስራ ቦታ አለመኖሩን እና በሴቶች ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥቶ አለመስራትንና የህጻናት ማቆያ ተሰርቶ አለማለቁን በእጥረት አስቀምጠዋል፡፡

በቀጣይም ኤጀንሲው ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተቀናጅቶ በመስራት ለስራ ዕድል ፈጠራ የተሰጡትን የመንግስትና የህዝብ ገንዘብ እና ከተሰጣቸው የጊዜ ገደብ በላይ የቆዩ ሼዶችን የማስመለስ ስራ በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባም ቋሚ ኮሚቴው አሳስቧል፡፡