(ዜና ፓርላማ) መጋቢት 02/2013 ዓ/ም፤ በሁለትዮሽ ውይይቱ የተገኙት በኢትዮጵያ የጃፓን አምባሳደር ኢቶ ታካኮ ሀገራቸው በተለያዩ ጊዜያት በገጠማት ተፈጥሯዊ አደጋ በተፈጠረው ሰብዓዊና ቁሣዊ ውድመት  ኢትዮጵያን ከጃፓን ህዝብና መንግስት ጎን  በመቆም የ5.4 ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ ማድረጓን አስታውሰው ለዚህም ምስጋና አቅርበዋል፡፡

በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ እና በኢትዮጵያ የጃፓን ኢምባሲ የሁለቱን ሀገራት የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት በሚያጠናክሩ ጭብጦች ዙሪያ ተወያይተዋል፡፡

በም/ቤቱ የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ እና ጃፓን በመልካምም ሆነ በክፉ አጋጣሚዎች ያላቸው ትብብር ጠንካራ እንደሆነ ገልጸው፤ በተለይ በአየር ንብረት ለውጥ፣ በፖለቲካና በኢኮኖሚው ዘርፍ የጀመሩትን አጋርነት አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ጠቁመዋል፡፡

ጃፓን በተለያዩ ተፈጥሯዊ አደጋዎች እየተፈተነችም ቢሆን ለኢትዮጵያ ሰብአዊ ድጋፍ ስለማድረጓ አመስግነው፤ በቀጣይ ለጃፓን የብርሃን ዘመን እንዲሆን መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል፡፡   

ኢትዮጵያ በታሪኳ በአፍሪካም ሆነ ከአፍሪካ ውጭ በሰላም ማስከበር ከመሳተፍ በስተቀር የትኛውንም ሀገር ሉአላዊነት እንደማትደፍር ያስረዱት የተከበሩ ነገሪ ሌንጮ (ዶ/ር)፤ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን በህዝብ ግፊት የመጣውን ለውጥ የሚፈታተኑ ዘመቻዎች በሀገር ውስጥና ከውጭ እየተስተዋሉ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

 ጃፓን በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል ያለውን ነባራዊ ሁኔታም ሆነ በህዳሴው ግድብ ላይ ኢትዮጵያ ያላትን ግልጽ አቋም ተረድታ ለሌሎች አካላት በማሳወቅ አጋርነቷን እድታሳይ ሲሉም አክለው ተናግረዋል፡፡

በሌላ በኩል አማባሳደሯ ሰሞኑን በትግራይ ክልል ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ለማጣራት ወደ ስፍራው ማምራታቸውን ገልጸው፤ የኢትዮጵያ መንግስት እና አለም አቀፍ ለጋሾች የተፈጠረውን ችግር ለመቅረፍ እያደረጉ ያለውን ጥረትም አድንቀዋል፡፡

የጃፓን መንግስት በትግራይ ክልል ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች ምግብና የህክምና አገልግሎትን ጨምሮ ለሌሎች ሰብዓዊ ድጋፎች የሚውል 6.6 ሚሊየን ብር ድጋፍ ማድረጉንና በቀጣይም ድጋፉን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አምባሳደሯ ቃል ገብተዋል፡፡

በተመሳሳይ ጃፓን እና ኢትዮጵያ በትምህርት፣ በጤና እንዲሁም በኢኮኖሚው ዘርፍ ያላቸውን ግንኙነት በማጠንከር፤ የግሉ ዘርፍም ተቀራርቦ እንዲሰራ ማበረታታት የሀገራቸው አቋም ስለመሆኑ አምባሳደሯ ጠቁመዋል፡፡       

በ አበባው ዮሴፍ