በኢፌዴሪ ህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በኢትዮጵያ አየር ኃይል የመስክ ምልከታ አድርጓል።

በቋሚ ኮሚቴው ሰብሳቢ በተከበሩ ዶ/ር ዲማ ነገዎ ለተመራው ልዑክ የኢፌዴሪ አየር ኃይል ዋና አዛዥ ሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ እና የአየር ኃይል ከፍተኛ አመራሮች አቀባበል አድርገውላቸዋል።

ሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ ለቋሚ ኮሚቴው አባላት ባደረጉት ገለፃ የኢትዮጵያ አየር ኃይል ሀገራዊ ለውጡን ተከትሎ ባደረጋቸው የሪፎርም ስራዎች በአቭዬሽን፣ በአየር መከላከል፣ በሰው ኃይል አቅም እና በመሰረተ ልማት ግንባታ ስኬት ተመዝግቧል።

አየር ኃይል በአሁን ወቅት በሁሉም ረገድ የተጣለበትን ሀገራዊ ኃላፊነት በብቃት መወጣት በሚችልበት የዝግጁነት ደረጃ ላይ እንደሚገኝም ዋና አዛዡ ሌተናል ጀኔራል ይልማ መርዳሳ ተናግረዋል።

በመስክ ምልከታቸው አየር ኃይል ህዝብና መንግስት የጣሉበትን አደራ በቁርጠኝነት እየተወጣ መሆኑን የገለፁት በኢፌዴሪ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ ዶ/ር ዲማ ነገዎ ተቋሙ ትልቅ አድናቆትና ምስጋና ሊቸረው ይገባል ብለዋል።