የውክልና ሥራ ለሕብረተሰቡ የልማት ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ በመስጠት ቁልፍ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ የተከበሩ ወይዘሮ መሠረት ኃይሌ ገለጹ
--------------------------
(ዜና ፓርላማ) መጋቢት 18 ፣ 2018 ዓ.ም፤ የውክልና ሥራ ሕብረተሰቡ ለሚያነሳቸው የልማት ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት ቁልፍ ሚና እየተጫወተ እንደሚገኝ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር ዴዔታ የተከበሩ ወ/ሮ መሰረት ኃይሌ ገልጸዋል።
ሚኒስትር ዴዔታዋ፤ ይህንን የገለፁት የየካቲት ወር የውክልና ሥራን አስመልክቶ ከየክልል አስተባባሪዎች ጋር ባደረጉት የውይይት መድረክ ላይ ሲሆን፣ የውክልና ሥራው በሕዝብና በመንግሥት መካከል ያለውን ግንኙነት በማጠናከር ለልማት ጥያቄዎች ምላሽ ለመስጠት ያለውን ስትራቴጂካዊ ፋይዳ አብራርተዋል።
በክልሎች የተካሄዱት የውክልና ሥራዎች መንግሥት የሕዝብን የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎች በቀጥታ አድምጦ አፋጣኝ ምላሽ የሚሰጥበት እና በሕዝብና በመንግሥት መካከል ጠንካራ ድልድይ ሆኖ የሚያገለግል እንደሆነ ሚኒስትር ዴዔታዋ ገልጸዋል።
በሌላ በኩል አስተባባሪዎቹ፥ የመንገድ ግንባታ ፕሮጀክቶች መጓተት፣ የዜጎችን ሰላምና ደኅንነት መረጋገጥ፣ የኑሮ ውድነት ተጽዕኖ፣ ለአርሶ አደሩ የግብርና ግብዓቶች አቅርቦት እጥረት፣ የነዳጅ ስርጭት እና ለሕገ-ወጥ ነጋዴዎች መጋለጥን ከመራጩ ጋር በነበራቸው ውይይቶች መነሳታቸውን ጠቅሰዋል።
እንዲሁም፥ የኤሌክትሪክ ሀይል መቆራረጥና ተደራሽነት አነስተኛ መሆን የሕዝቡ መሰረታዊ ጥያቄዎች መሆናቸውንም በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የክልል የውክልና ስራ አስተባባሪዎች አንስተዋል።
የተከበሩ ወ/ሮ መሰረት ኃይሌ በሰጡት ምላሽ፣ መንግሥት በሕዝብ ውክልና ለተነሱ ጥያቄዎች ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እንደሚሠራና ጥያቄዎቹ ተደራጅተው ለሚመለከታቸው አስፈጻሚ ተቋማት በመላክ ክትትልና ቁጥጥር እንደሚደረግባቸውም ነው ያብራሩት።
እንዲሁም የኮሪደር ልማት ያስገኛቸውን ተጨባጭ ውጤቶች ይበልጥ በማስፋት የሕዝብን ተጠቃሚነት ማረጋገጥና የሰንበት ገበያዎችን በማጠናከር የኑሮ ውድነትን ማቃለል የመንግሥት የቤት ሥራዎች መሆናቸውንም ጠቁመዋል።
ከዚህ ባለፈ የውክልና ሥራ ተቋማዊ በሆነ መንገድና በተቀናጀ አሠራር እንዲመራ መደረጉ፣ ሕዝቡ መንግሥት እየሠራቸው ስላሉ ተግባራት በቂ መረጃ እንዲኖረው ከማስቻሉም በላይ የመንግሥት ተቋማት ለሕዝብ ጥያቄ ምላሽ የመስጠት አቅማቸውን እንዲያሳድጉ ትልቅ ዕድል የፈጠረ መሆኑን ሚኒስትር ዴዔታዋ አስረድተዋል።
በተጨማሪም አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ለማዘመንና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን የዲጂታል ቴክኖሎጂ ትግበራ ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው ገልጸዋል።
በመጨረሻም የፋይዳ መታወቂያና የመሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መጀመር የቢሮክራሲ ማነቆዎችን በመፍታት ለዜጎች ቀልጣፋ አገልግሎት ለመስጠት እንዳስቻለም የተከበሩ ወ/ሮ መሠረት ተናግረዋል።
( በ-ሚፍታህ ኪያር )




ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/@FDREHOPR
በቴሌግራም
በትዊተር
በዌብሳይት
www.hopr.gov.et ይከታተሉ።