ምክር ቤቱ የባለብዙ ተዋንያን የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎትና አስተዳደር ረቂቅ አዋጅን መርምሮ አፀደቀ
----------------------
(ዜና ፓርላማ) መጋቢት 29 ፣ 2018 ዓ.ም፤ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ14ኛ መደበኛ ስብሰባው የባለብዙ ተዋንያን የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎትና አስተዳደር ረቂቅ አዋጅን መርምሮ አጽድቋል፡፡
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ ሰለሞን ላሌ ሪፖርት እና የውሳኔ ሀሳብ አቅርበዋል፡፡
ረቂቅ አዋጁ በመንግስት ብቻ የሚሰጠው የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎት በቂ ባለመሆኑ ወቅቱ የሚጠይቀውን የባለብዙ ተዋንያን የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎት ሥርዓት እንዲዘረጋ ምቹ መደላድል እንደሚፈጥር ሰብሳቢው አመላክተዋል፡፡
በዲጂታል ግብርና ኤክስቴንሽን የሚያማክሩ እና የመረጃ ቅብብሎሽ አገልግሎት የሚሰጡ የግል ባለሀብቶች ፣መንግስታዊ ያልሆኑ እና የሆኑ ድርጅቶች እየታዩ በመሆኑ በግብርና ኤክስቴንሽን ውስጥ አገልግሎት እንዲሰጡ የሚያስችል ረቂቅ አዋጅ መሆኑን የተከበሩ አቶ ሰለሞን ላሌ አያይዘው አስገንዝበዋል፡፡
የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎት አሰጣጡ ጥራትና ፍትሃዊነት ቁጥጥር ትኩረት የሚሻ በመሆኑ አገልግሎት የሚሰጠው በተመዘገበና የብቃት ማረጋገጫ ባገኘ አገልግሎት አቅራቢ መሆን እንደሚኖርበት አዋጁ የአሰራር ሥርዓት እንዳስቀመጠ ጠቁመዋል፡፡
የግብርና ኤክስቴንሽን መሰረት ልማት ዝርጋታዎችን ማዘመን በመንግስት ላይ ብቻ በመውደቁ በሚጠበቀው ደረጃ እርካታ ያልተገኘበትን የተጠቃሚዎች ፍላጎት ምላሽ ለመስጠት የግብርና ኤክስቴንሽን ፈንድ ለማቋቋምና ፍላጎት ለመቅረፍ ረቂቅ አዋጁ እንዳካተተ ሰብሳቢው አንስተዋል፡፡
በግብርና ባለሙያዎች ብቻ ይሰጥ የነበረው የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎት አሁን ላይ የምርት መጠንና ምርታማነትን ለማሳደግ በቂ ምላሽ ባለመስጠቱ ይህንን ችግር ለመፍታት አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎቱን ለማሻሻልና ለማዘመን ረቂቅ አዋጁ አስፈላጊ ነው ብለዋል፡፡
የሀገራችን ኢኮኖሚ በግብርና ላይ የተመሰረተ መሆኑን የጠቀሱት አቶ ሰለሞን ላሌ፣ በዘርፉ ምርትን በብዛት፣ በጥራትና በቀጣይነት ለማሳደግ የግብርና ኤክስቴንሽን ከፍተኛ ሚና እንዳለው ገልጸዋል፡፡
የምክር ቤት አባላት በበኩላቸው፣ ከግብርና ምርምር የሚገኙና ከውጭ የሚመጡ ቴክኖሎጂዎችን የግብርና ባለሙያው ለአርሶ አደሮች በተግባር ማሳ ላይ እያሳዩና እያስተማሩ አገልግሎት መስጠት እንዳለባቸው አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
የምክር ቤት አባላቱ አያይዘውም የግብርና ኤክስቴንሽን ተደራሽነት ከ36% በላይ አለማለፉን ጠቁመው፣ ረቂቅ አዋጁ ይህንን ክፍተት እንደሚሞላ ገልጸዋል፡፡
ረቂቅ አዋጁ መንግስታዊ ያልሆኑ የአገልግሎት ተዋንያን ህጋዊነትን በጠበቀ መልኩ፣ ተጠያቂነት በሰፈነበት እና ጥራቱ በጠበቀ ሁኔታ መንግስትን እና አርሶ አደሩን በመደገፍ የግብርና ልማቱን በሚገባ እንደሚያሳልጥ ጠቁመዋል።
በመጨረሻም ምክር ቤቱ በረቂቅ አዋጁ ላይ ሰፊ ውይይት ካደረገ በኋላ፣ የባለብዙ ተዋንያን የግብርና ኤክስቴንሽን አገልግሎትና አስተዳደር ረቂቅ አዋጅን፣ አዋጅ ቁጥር 1411/2018 ሆኖ በሙሉ ድምጽ አጽድቆታል፡፡
(በ አገሪቱ ጌቴ)






ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/@FDREHOPR
በቴሌግራም
በትዊተር
በዌብሳይት
www.hopr.gov.et ይከታተሉ።