የሀገር ውስጥ የስኳር ፍጆታን በማሟላት ወደ ዓለም ገበያ መግባት እንደሚገባ ቋሚ ኮሚቴው አሳሰበ

------------------------

(ዜና ፓርላማ) መጋቢት 23 2018 .ም፣ አዲስ አበባ፤ ከውጭ ሀገር የሚገባውን የስኳር ምርት ከማስቀረትና የሀገር ውስጥ ፍጆታን ከመሸፈን በተጨማሪ የስኳር ምርትን ወደ ውጭ በመላክ የዓለም ገበያ ሰብሮ ለመግባት የስኳር ፋብሪካዎች አቅደው ሊሠሩ እንደሚገባቸው በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳስቧል፡፡

ቋሚ ኮሚቴው ይህንን ማሳሰቢያ የሰጠው፤ የኢትዮጵያ ስኳር ኢንዱስትሪ ግሩፕን 2018 በጀት ዓመት 6 ወራት የእቅድ አፈጻጸም ሪፖርት በገመገመበት ወቅት ነው።

የመንግሥት ልማት ድርጅቶች ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ መለሰ መና በሰጡት አስተያየት፣ ከውጭ ሀገር የሚገባውን ስኳር ለማስቀረትና የሀገር ውስጥ ፍጆታን ለመሸፈን የስኳር ፋብሪካዎች በትኩረት ሊሠሩ እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡

የተከበሩ አቶ መለሰ መና አክለውም የሀገር ውስጥ የስኳር ፍጆታን መሸፈን ብቻ ሳይሆን ኢትዮጵያ ስኳርን ወደ ውጭ ሀገር በመላክ የዓለም ገበያ ሰብራ እንዲትገባ የስኳር ፋብሪካዎቹ አቅደው ሊሠሩ እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡

ከስኳር ፋብሪካዎች የሚወጡትን ተረፈ ምርቶች ጥቅም ላይ ለማዋል ከብሔራዊ አረቄ ፋብሪካና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት መሥራት እንደሚያስፈልግም ሰብሳቢው ጨምረው አስገንዝበዋል፡፡

የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ የተከበሩ ኢንጅነር ስለሺ ኮሬ (/) በበኩላቸው የስኳር ምርትን በማሳደግ በስንዴ ምርት የመጣውን እምርታ መድገም እንደሚቻል ጠቁመዋል፡፡

የስኳር ፋብሪካዎች አርጅተው ወደ ችግር ከመግባታቸው በፊት ከወዲሁ የስኳር ፋብሪካዎቹ አቅደው ሊሠሩ እንደሚገባም ምክትል ሰብሳቢው ጨምረው አሳስበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ስኳር ኢንዱስትሪ ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ወዩ ሮባ በሰጡት ማብራሪያም የስኳር ፋብሪካዎች ስኳር ለማምረት የሚፈጅባቸውን ጊዜ በማሳጠር ስኳርን በአጭር ጊዜ ለማምረት ጥረት እያደረጉ ቢሆንም በተለይ አዳዲስ የስኳር ፋብሪካዎች ሲገነቡ ያላካተቷቸው ነገሮች ስላሉ ለማሟላት ጥረት እየተደረገ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

ባለድርሻ አካላት ተረፈ ምርቶችን ከአንድ የስኳር ፋብሪካ ብቻ ለመግዛት ስለሚልጉ እንጂ የስኳር ፋብሪካዎች የተረፈ ምርት ስርጭት ችግር ስለሌለባቸው ከአረቄ ፋብሪካዎችና ለሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር ለመሥራት ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

( ጋሹ ይግዛው)

ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament

በዩቲዩብ

https://www.youtube.com/@FDREHOPR

በቴሌግራም

https://t.me/ParlamaNews

በትዊተር

http://twitter.com/fdrehopr

በዌብሳይት

www.hopr.gov.et ይከታተሉ።