"ሀገራዊ የምክክር ጉባኤው በስኬት በመጠናቀቁ እንኳን ደስ አለን" የተከበሩ አፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ"

---------------------

(ዜና ፓርላማ) ነሐሴ 16 2018 .ም፤ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ-ጉባኤ አቶ ታገሰ ጫፎ፣ የሀገራችንን ዘላቂ ሰላም፣ አንድነት እና አብሮነት በጽኑ መሠረት ላይ ለማቆም ያለመው ታሪካዊው ሀገራዊ የምክክር ጉባኤ በስኬት መጠናቀቁን በማስመልከት ለመላው ኢትዮጵያውያን የእንኳን ደስ አላችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።

አፈ-ጉባኤው በመልዕክታቸው፣ ይህ ጉባዔ ለነገዋ ጠንካራ ኢትዮጵያ መሠረት የተጣለበት እና የሀገራችን የወደፊት ዕጣ ፈንታ በጋራ የተቀረጸበት ታሪካዊ ምዕራፍ መሆኑን ገልጸዋል።

የዚህ የምክክር ሂደት ዋና ዓላማ በሀገራችን ለረጅም ጊዜያት የግጭት መነሻ የሆኑ መሠረታዊ ሀገራዊ ጉዳዮችን በውይይት መፍታት መሆኑን ያነሡት አቶ ታገሰ፣ ምክክሩ በኢትዮጵያ ታሪክ የመጀመሪያው አካታች እና አጠቃላይ ሀገራዊ መድረክ መሆኑ ልዩ እንደሚያደርገው አስረድተዋል።

የምክክር ሂደቱ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በወጣው አዋጅ ቁጥር 1265/2014 መሠረት ራሱን የቻለ እና ገለልተኛ የፌዴራል መንግሥት አካል ሆኖ በተቋቋመው የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን አማካይነት በሕጋዊ ሥርዓት መመራቱን አፈ-ጉባኤው አስታውሰዋል።

ኮሚሽኑ ሥራ ከጀመረበት ጊዜ አንሥቶ እስከ ወረዳ እና ቀበሌ ድረስ በመውረድ አርብቶ አደሮችን፣ አርሶ አደሮችን፣ ሴቶችን፣ ወጣቶችን፣ አካል ጉዳተኞችን፣ የሃይማኖት ተቋማትን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎችን፣ የሲቪክ ማኅበራትን እና ዳያስፖራውን ያካተተ ሰፊ ሥራ ማከናወኑ የምክክሩን ተአማኒነት እና ሕዝባዊ ቅቡልነት ማረጋገጡን አብራርተዋል።

ከሕዝብ እና ከባለድርሻ አካላት በተሰበሰቡ አጀንዳዎች መሠረት ተለይተው በቀረቡ ስምንት ዐበይት ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ ከመላው ሀገራችን የተውጣጡ 4,000 በላይ ተሳታፊዎች በሰላማዊ እና ዴሞክራሲያዊ መንገድ ሰፊ ምክክር በማድረግ የጋራ መግባባት ላይ መድረሳቸው ተገልጿል።

በዚህም የኃይል እና የጦርነት ፖለቲካን በማስቀረት ችግሮችን በጠረጴዛ ዙሪያ መፍታት እንደሚቻል ማሳየት መቻሉን አፈ-ጉባኤው አጽንኦት ሰጥተዋል።

ጉባዔው በስኬት ሲጠናቀቅ ለሀገራችን ዘላቂ መፍትሔ የሚሆኑ በርካታ ዐበይት ምክረ ሐሳቦች መፍለቃቸውን የጠቆሙት አቶ ታገሰ ጫፎ፣ እነዚህ ምክረ ሐሳቦች ለቀጣይ የፖሊሲ ማሻሻያዎች፣ ለሕገ-መንግሥታዊ እና ተቋማዊ ለውጦች፣ እንዲሁም ለዘላቂ እርቅ እና ብሔራዊ መግባባት መሠረት የሚጥሉ መሆናቸውን አስገንዝበዋል።

የምክክሩ ዋነኛ ግብ የትናንት ታሪካዊ ስብራቶችን በማከም ለቀጣዩ ትውልድ ሰላሟ የተጠበቀ እና ብልጽግናዋ የተረጋገጠ ሀገር ማስረከብ በመሆኑ፣ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ፣ የፖለቲካ ኃይሎች እና የመንግሥት አካላት ከምክክሩ የተገኙ ውጤቶችን በባለቤትነት በመጠበቅ ወደ ተግባር እንዲተረጉሟቸው አፈ-ጉባኤው ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

ለዚህ ታሪካዊ ምዕራፍ ስኬት አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላትም በራሳቸው እና በምክር ቤቱ ስም ምስጋና አቅርበዋል።

ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament

በዩቲዩብ

https://www.youtube.com/@FDREHOPR

በቴሌግራም

https://t.me/ParlamaNews

በትዊተር

http://twitter.com/fdrehopr

በዌብሳይት

www.hopr.gov.et ይከታተሉ።

See less