“በኢትዮጵያ እና ሕንድ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት አዲስ ምዕራፍ የተከፈተበት ወቅት ነው”
------ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ ------
(ዜና ፓርላማ) ታህሳስ 08 ፣ 2018 ዓ.ም፤ የሕንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፣ ዛሬ በሕዝብ ተወካዮች እና በፌዴሬሽን ምክር ቤት የጋራ ስብሰባ ላይ በመገኘት መልዕክት አስተላልፈዋል።
በመልዕክታቸው ሁለቱ የጥንታዊ ሥልጣኔ ባለቤት አገራት መካከል ያለው ግንኙነት ወደ ስትራቴጂክ አጋርነትና አዲስ ምዕራፍ የተሸጋገረበት ወቅት ላይ እንገኛለን ብለዋል።
ባለፉት ዓመታት ሁለቱ አገራት በኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ዲፕሎማሲያዊ ዘርፎች ያላቸው ግንኙነት ማደጉን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
ሕንዳውያን ባለሀብቶች በጤና፣ በግብርና እና አምራች ዘርፎች ከ 5 ቢሊየን ዶላር በላይ ኢንቨስት በማድረግ ላይ እንደሚገኙም ተናግረዋል።
ሁለቱ አገራት በያሉበት አህጉር ተፅህኖ ፈጣሪ መሆናቸውን ገልጸው ለጋራ ተጠቃሚነትና ብልፅግና በስትራቴጂካዊ ትብብር በጋራ እንሰራለን ብለዋል።
ኢትዮጵያ የብሪክስ አባል ሀገር እንድትሆን ሕንድ ድጋፍ ማድረጓንም ጠቁመዋል።
በርካታ ኢትዮጵያዊያን በሕንድ የትምሀርት ዕድል አግኝተዋል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአየር ንብረት ለውጥ በመከላከል፣ በጤና በግብርና፣ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ በጋራ ለመሥራት ዝግጁ ነን ብለዋል።
አዲስ ሐሳቦችን ለሚያፈልቁ የሥራ ፈጣሪ ወጣቶችና ተቋማትን መገንባትና ማበረታታት የኢትዮጵያን መጪ ዘመናት የሚቀይርና የሚወስን ነው ሲሉም ተናግረዋል።
በዚህ ታላቅ ምክር ቤት ውስጥ ሕጎቻችሁ ይወጣሉ፤ እዚህ ውስጥ የሕዝቡ መሻት የመንግሥት መሻት ይሆናል ያሉ ሲሆን በውይይትና ዲሞክራሲያዊ መንገድ የህግ የበላይነትን ማክበር ይገባል ሲሉ ተናግረዋል።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ለተደረገላቸው የክብር አቀባበልና ለተበረከተላቸው የኢትዮጵያ ታላቁ የክብር ኒሻን ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ አመስግነዋል።
(በ በለጠ ሙሉጌታ)
ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/@FDREHOPR
በቴሌግራም
በትዊተር
በዌብሳይት
www.hopr.gov.et ይከታተሉ።