የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የእፅዋት ጥበቃ እና ኳራንታይን ረቂቅ አዋጅን አፀደቀ
-----------------
(ዜና ፓርላማ) ታህሳስ 14፣ 2018 ዓ.ም፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በ5 ኛ ዓመት የሥራ ዘመኑ በ5ኛ መደበኛ ሥብሰባው የእፅዋት ጥበቃ እና ኳራንታይን ረቂቅ አዋጅን መርምሮ አፅድቋል::
የግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ ሰለሞን ላሌ ረቂቅ አዋጁን አስመልክቶ ቋሚ ኮሚቴው ያዘጋጃውን ሪፖርትና የውሳኔ ሃሳብ ያቀረቡ ሲሆን ረቂቅ አዋጁ ከጊዜ ወደ ጊዜ በፍጥነት እየተሻሻሉና እየተለወጡ የመጡትን ዓለም አቀፋዊ የእፅዋት ጥበቃ እና ኳራንቲን ደረጃዎችና አሰራሮች በመከተል ከዓለም አቀፉ ማህበረሰብ ጋር የተናበበ ቀልጣፋ እና ውጤታማ ሥራ ለመስራት መደላድል የሚፈጥር መሆኑን አንስተዋል::
የተከበሩ አቶ ሰለሞን አያይዘውም አግባብነት ያለውና ደረጃውን የጠበቀ የተባይ አሰሳና ቅኝት ሥጋት ትንተና ለማድረግ እና በመግቢያ በሮች የገቢና ወጭ እፅዋት ፤ የእፅዋት ውጤት እና ሌሎች ቁጥጥር የሚደረግባቸው ቁሶችን በተገቢው ለመቆጣጠር የሚያስችል ማዕቀፍ ያለው መሆኑን እንዲሁም ዘመናዊ የተባይ መከላከል እና መቆጣጠር ሥርዓትን በመዘርጋት ምርታማነትንና የምርት ጥራትን በማሳደግ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተጠቃሚነት በማረጋገጥ ረገድ ከፍተኛ ፋይዳ ያለው መሆኑን አስረድተዋል።
ፈቃድ ሳያወጡ ወይም ህጋዊ ባልሆነ መንገድ በአየር እና በየብስ ከእፅዋትና የእፅዋት ውጤቶች ጋር የሚገቡ ተባዮችን ለመከላከል አዋጁ ያስቀመጠው የመከላከያ መንገድ ስለመኖሩ፣ ከእፅዋትና ከእፅዋት ውጤቶች ጋር ተባዮች ብቻ ሳይሆኑ አረሞችም የሚገቡበት ሁኔታ ስላለ ተባይ በሚል ብቻ የተቀመጠበትን ምክንያት በተመለከተ እንዲሁም ሌሎች በርካታ ጥያቄዎች ከምክር ቤት አባላት የተነሱ ሲሆን በግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሰቢ በተከበሩ አቶ ሰለሞን ላሌ ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል::
ምክር ቤቱ በረቂቅ አዋጁ ላይ ሰፊ ውይይት ካደረገ በኋላ የእፅዋት ጥበቃ እና ኳራንታይን አዋጅ ቁጥር 1420/ 2018 በማድረግ በሙሉ ድምጽ አፅድቆታል።
ምክር ቤቱ በ4ኛ ዓመት የስራ ዘመኑ ሰኔ 5 ቀን፣ 2017 ዓ.ም ባካሄደው 36ኛ መደበኛ ስብሰባ የእፅዎት ጥበቃ እና ኳላንታይን ረቂቅ አዋጅን ለዝርዝር እይታ ለግብርና ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ መምራቱ ይታወሳል።
(በፀሀይ ነጋሽ)
ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/@FDREHOPR
በቴሌግራም
https://t.me/ParlamaNews
በትዊተር
http://twitter.com/fdrehopr
በዌብሳይት
www.hopr.gov.et ይከታተሉ።