ሚያዝያ 13/ 2018

የሴኩዩሪቲ አገልግሎት ክፍያ አካትቶ የተሻሻለው የኢትዮጵያ አቭየሽን ሴኩሪቲ አዋጅ ፀደቀ።

የህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው መደበኛ ስብሰባው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለሚሰጠው የአቭየሽን አገልግሎት ከተገልጋዮች ክፍያ መስብሰብ የሚያስችለውን አዋጅ በአብላጫ ድምፅ አፅድቋል።

በአየር ትራንስፖርት ስርዓቱ የሚቃጡ የሕገ ወጥ ጣልቃ ገብ ድርጊቶች፣ ባህሪያትና የአፈፃፀም ስልት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገና እየተወሳሰበ በመምጣቱ፤ ነባሩ አዋጅ ከሃያ ዓመታት በላይ ሳይሻሻል የቆየ በመሆኑ፤ ዘመን ያመጣቸውን ውስብስብ ህገ ወጥ ጣልቃ ገብ ድርጊቶችን ለመቆጣጠር የሚያስችል እንዲሁም ወቅቱን የዋጀ የህግ ማዕቀፍ መደንገግ የሚያስፈልግ በመሆኑ አዋጁን ማሻሻል እንዳስፈለገ ተነግሯል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ የዓለም አቀፍ ሲቪል አቭዬሽን ድርጅት ከራሱ መንገደኞች፣ ከሌሎች ኦፕሬተሮች እና በኤርፖርት ውስጥ የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አገልግሎት ከሚያገኙ ማናቸውም አካላት የአገልግሎት ክፍያ በመሰብሰብ ለብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ገቢ እንዲያደርግ በአዋጁ ተደንግጓል።

ከአገልግሎት ክፍያ የሚሰበሰበው ገቢ ለኤርፖርት የሴኩዩሪቲ ቴክኖሎጂ ግዢ፣ ለአቭዬሽን ሴኩዩሪቲ የፀጥታ አካላት ሥልጠናና አቅም ግንባታ፣ ለአነፍናፊ ውሻ ግዥና ሥልጠና፣ ለጥገናና ማስፋፊያ እንዲሁም አሠራርን ለማዘመን የሚውል መሆኑም በአዋጁ ተካትቷል።

ምንታምር ፀጋው