"ወጣቶች የሀገራችን የነገ ተሰፋዎች ብቻ ሣይሆኑ የዛሬም የልማት ሞተሮች ናቸው"
------ የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ በዶ ----
(ዜና ፓርላማ) ታህሳስ 14፣ 2018 ዓ.ም፤ በኢትዮጵያ የሚገኙ አፍላ-ወጣቶችና ወጣቶች የሀገሪቱ ተሰፋዎች ብቻ ሣይሆኑ የዛሬም የልማት ሞተሮች ናቸው ሲሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምክትል አፈ-ጉባዔ የተከበሩ ወ/ሮሎሚ በዶ ገለጹ።
ወጣቶች በቀጣይ ሀገር ተረካቢ ዜጎች መሆናቸውን መንግሥት በጽኑ በማመን ከወዲሁ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ እንደሆነም የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ አስገንዝበዋል።
አፈ-ጉባኤዋ ይህንን ያሉት "Harnessing the Population Dividend by Investing in Ethiopia Youth” በሚል ርዕስ ላይ በአ..ፌ.ዲ.ሪ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት፥ በዲ.ኤስ.ደብሊው (DSW) ኢትዮጵያ እና ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ምሁራን ጋር የምክክር መድረክ በተካሄደበት ወቅት ነው።
ወጣቶች በትምህርት፣ በሥራ ዕድል እና በሌሎች ተጓዳኝ አገልግሎቶች የሚደገፉ ከሆነ ለሀገር ሁለንተናዊ እድገትና ብልጽግና እንዲሁም ለዘላቂ ልማት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከት ይችላሉ ሲሉ አፈ-ጉባዔዋ ገልጸዋል።
ወጣቶች አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች የመፍጠርና የመቀበል እንዲሁም አዳዲስ ሀሳቦችን በማመንጨት የመፍትሔ ሐሳብም የሚያመጡ በመሆኑ ለሀገር ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ትልቅ የለውጥ ዕድል መሆን ይችላሉ ብለዋል።
በምክር ቤቱ የጤና፣ ማህበራዊ ልማት፣ ባሕልና ስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የተከበሩ ወርቀሰሙ ማሞ በበኩላቸው፤ ወጣቶችና አፍላ ወጣቶች የሀገሪቱን ብሄራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ የላቸው ሚና ከፍተኛ መሆኑን አመላክተዋል።
ወጣቶች በኢትዮጵያ ማህበራዊ፣ ምጣኔ ሀብታዊ እና ፖሊቲካዊ ጉዳዮች ላይ የሚያደርጉትን ተሳትፎና ተጠቃሚነት ለማሳደግ የሚያስችሉ ምቹ ሁኔታዎችን መፍጠር እንደሚያስፈልግም የተከበሩ ወ/ሮ ወርቅሰሙ አስረድተዋል።
በምክክር መድረኩ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ የዲ.ኤስ.ደብሊው (DSW) ኢትዮጵያ የስራ ሀላፊዎች የተገኙ ሲሆን የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ምሁራን በወጣቶች ዙሪያ የተሰሩ የተለያዩ ጥናታዊ ጹሁፎችን እያቀረቡ ይገኛሉ።
(በሚፍታህ ኪያር)
ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ https://www.youtube.com/@FDREHOPR
በቴሌግራም https://t.me/ParlamaNews
በትዊተር http://twitter.com/fdrehopr
በዌብሳይት www.hopr.gov.et ይከታተሉ።