ረቂቅ አዋጁ በአቬሽን ደህንነት ረገድ የኢትዮጵያን ከፍታ የሚያረጋግጥ መሆኑ ተገለጸ
---------------------
(ዜና ፓርላማ) የካቲት 10 ፣ 2018 ዓ.ም ፤ የኢትዮጵያ የአቬሽን ሴኪዩሪቲ ረቂቅ አዋጅ በአቬሽን ደህንነት ረገድ የኢትዮጵያን ከፍታ የሚያረጋግጥ መሆኑን በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አስንዝቧል፡፡
ቋሚ ኮሚቴው በኢትዮጵያ የአቬሽን ሴኪዩሪቲ ማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ተወያይቷል፡፡
ረቂቅ አዋጁ ቀደም ሲል በዋናነት ለውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ እና በተባባሪነት ለከተማ መሰረተ-ልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ለዝርዝር እይታ መመራቱ ይታወሳል፡፡
በውይይቱም ከባለድርሻ አካላት ግልጽነት ያስፈልጋቸዋል የተባሉ አስተያየቶችና ጥያቄዎች ተነስተው በብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት የስራ ኃላፊዎች ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቶባቸዋል፡፡
የከተማ መሰረተ-ልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ ፕሮፌሰር መሀመድ አብዶ በሰጡት አስተያየት ረቂቅ አዋጁ በአቬሽን ደህንነት ዘርፍ የኢትዮጵያ አየር መንገድን ደረጃ ከፍ በማድረግ ረገድ ፋይዳው ከፍተኛ ስለሆነ ግልፅነት የጎደላቸውን ቃላት በማስተካከል ጸድቆ ወደ ተግባር እንዲገባ ጥረት መደረግ አለበት ብለዋል፡፡
የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ፈቲህ መሀዲ (ዶ/ር) በበኩላቸው አዋጁ በጥራቱና በቅልጥፍናው የአቬሽን ደህንነትን የበለጠ የሚያጠናክር እና የኢትዮጵያ አየር መንገድ አለም አቀፍ የአቬሽን ደህንነት መመዘኛን በማሟላት ቀዳሚ ሆኖ እንዲቀጥል ያስችላል ብለዋል፡፡
የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ሲሳይ ቶላ በበኩላቸው በአየር ትራንስፖርት ስርዓቱ የሚቃጡ የሕገ-ወጥ ድርጊቶች ባህሪያትና የአፈፃፀም ስልት ከግዜ ወደ ግዜ እያደገና እየተወሳሰበ በመምጣቱ የአቭዬሽን ደህንነት ስጋቶችን በብቃትና በጥራት መከላከል እንዲያስችል ቀደም ሲል የነበረው የአቭዬሽን ሴኩዩሪቲ አዋጅ ቁጥር 432/1997 ማሻሻል አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል ብለዋል።
(በድረስ ገብሬ)
ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/@FDREHOPR
በቴሌግራም
በትዊተር
በዌብሳይት
www.hopr.gov.et ይከታተሉ።