"ነፃ፣ ገለልተኛና ጠንካራ ተቋማትን መገንባት ለተሳካ ሀገረ መንግሥት ግንባታ የላቀ ሚና አለው "
-----የተከበሩ አቶ ታገሰ ጫፎ-----
(ዜና ፓርላማ) የካቲት 25 ፣ 2018 ዓ.ም፤ ተቋማትን መገንባት ሀገርን መገንባት ነው ሲሉ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈጉባኤ የተከበሩ አቶ ታገሰ ጫፎ ገልፀዋል።
የተከበሩ አቶ ታገሰ ጫፎ ይህን ያሉት "የዳኝነትና ዴሞክራሲ ተቋማት እመርታ፤ ለተሳካ ሀገረ መንግሥት ግንባታ!" በሚል ርዕስ ለምክር ቤቱ ተጠሪ የሆኑ የዳኝነትና የዲሞክራሲ ተቋማት ያከናወኗቸውን ዓበይት ተግባራት ለተሳታፊዎች አቅርበው ሰፊ ውይይት በተደረገበት መድረክ ላይ ነው።
በውይይት መድረኩ ላይ ነፃ፣ ገለልተኛ ጠንካራ ተቋማትን መገንባት ለተሳካ ሀገረ መንግሥት ግንባታ የላቀ ሚና አላቸው ሲሉ አፈጉባኤው አፅንኦት ሰጥተዋል።
በመሆኑም ተቋማቱ ነፃና ገለልተኛ እንዲሆኑና ሙያዊ በሆነ መንገድ እንዲመሩ ብሎም አቅምና ስልጣን ኖሯቸው እንዲሰሩ ከሕግ ማዕቀፍ ጀምሮ የማሻሻል ስራዎች መሠራታቸውን አስታውሰዋል።
እነዚህ ስራዎች በመሰራታቸውም የዳኝነትና ዴሞክራሲ ተቋማት ላይ የተገኘው አዎንታዊ ውጤት ቀላል እንዳልሆነ ጠቁመዋል።
የተቋማቱን አቅም በማላቅ ደረጃ ተጨማሪ ድጋፎችን አጠናክረን መቀጠል አለብን ብለዋል።
በተለይ አገራችን ከፊት የሚጠብቃት 7ኛው ሀገር አቀፍ ምርጫ ነፃ፣ ፍትሀዊ፣ ተአማኒና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ እንዲተገበር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከ6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ተሞክሮን በመውሰድ በዴሞክራሲያዊ ምርጫ የላቀ አፈፃፀም እንዲኖራት እየሰራ ያለው ስራ የሚበረታታ መሆኑን ገልጸዋል።
መንግሥትም በምክር ቤቱ ለሀገር የሚጠቅሙ አማራጭ ሀሳቦች ተበራክተው እንዲታዩና ዋጋ እንዲኖራቸው የጀመረውን መንግሥታዊ ኃላፊነት የመወጣት ጉዞ ያጠናክራል ብለዋል።
በተመሳሳይ የሀገርን የዘመናት ውዝፍ የአለመግባባት መንገድ ጠራጊ የሆኑ እጅግ በጣም ወሳኝ ጉዳዮችን በአጀንዳነት ለይቶ በሀገራዊ ምክክር ለመፍታት የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን እየሰራ ያለው ስራ የሀገርን ችግር በመሰረታዊነት በመቅረፍ የሽግግር ፍትህን በማስፈን ረገድ ፋይዳው የጎላ መሆኑን አፅንኦት ሰጥተዋል።
ለዚህም ሁነት መሳካት ቀሪ ስራዎች ላይ ትኩረት በማድረግ የሀገርን ቁስል የማሻርና የማሻገር ስራን እውን ማድረግ የማይታለፍ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል።
እንዲሁም የዳኝነትና የዴሞክራሲ ተቋማቱ ከለውጡ በፊት የነበረባቸውን ክፍተት ቀርፈው በለውጥ ውስጥ እየተጓዙና ተቋም እያፀኑ ነገ መዳረሻቸውን ከክፍተት ለማፅዳት የጀመሯቸው ዘርፈ ብዙ ስራዎች የሚበረታቱ ናቸው ብለዋል።
ከዚህ ባለፈ ከተሳታፊዎች ለተነሱ አስተያየቶችና ጥያቄዎች የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት፣ የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ፣ የፌዴራል ዋና ኦዲተር መ/ቤት፣ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን እና የኢትዮጵያ ሕዝብ ዕንባ ጠባቂ ተቋም ከፍተኛ ኃላፊዎች ዝርዝር ምላሽና ማብራሪያዎችን ሰጥተዋል።
በውይይት መድረኩ ላይም ም/አፈ-ጉባኤ የተከበሩ ወ/ሮ ሎሚ በዶ፣ የመንግስት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር ተስፋዬ በልጅጌ (ዶ/ር)፣ የመንግስት ረዳት ተጠሪ ሚኒስትር የተከበሩ ወ/ሮ መሰረት ኃይሌ፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አመራርና አባላት፣ ሚኒስትሮች፣ የየተቋማት ኃላፊዎች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተሳትፈዋል።
(በ-ተስፋዬ ሚደቅሳ )
ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/@FDREHOPR
በቴሌግራም
በትዊተር
በዌብሳይት
www.hopr.gov.et ይከታተሉ።