በሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶች የክዋኔ ኦዲት የተገኙ ክፍተቶች እንዲታረሙ ቋሚ ኮሚቴው አሳሰበ
-------------------------
(ዜና ፓርላማ) ታህሳስ 02፣ 2018 ዓ.ም.፤ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግስት ወጪ አስተዳደር እና ቁጥጥር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ፕላን ልማት ሚኒስቴር በሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶች የክዋኔ ኦዲት የተገኙ ክፍተቶች እንዲታረሙ በትኩረት መስራት እንዳለበት አስገንዝቧል፡፡
ቋሚ ኮሚቴው በዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ፕሮጀክቶች የኦዲት ግኝትን መሰረት በማድረግ ከፕላን ልማት ሚኒስቴር ጋር ውይይት አድርጓል።
ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ የሺመቤት ደምሴ (ዶ/ር) ቋሚ ኮሚቴው በፌዴራል ዋና ኦዲተር የክዋኔ ኦዲት ግኝትን በግብአትነት በመጠቀም ክፍተቶችን በመለየት ማስተካከያ እንዲደረግ ሲሉ አሳስበዋል፡፡
የተከበሩ የሺመቤት ደምሴ (ዶ/ር) አዋጁ በትኩረት ተገምግሞ የህግ ማዕቀፎች ሊሟሉለት እንደሚገባ አመላክተው፣ ለክዋኔ ኦዲቱ የድርጊት መርሀ-ግብር ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ማዘጋጀት እንዳለበት አሳስበዋል።
የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ የተከበሩ ወ/ሮ አራሬ ሞሲሳ በተዘረጋው አሰራር መሰረት ከኦዲት ግኝቱ በኋላ የተሰሩ ስራዎች በእቅድ ተይዘው መተግበር እንዳለባቸው ተናግረዋል።
በሌላ በኩል የፋይናሽያል እና የፊዚካል ሪፖርት የማያቀርቡ ፕሮጀክቶች፤ በተቀመጠላቸው ጊዜ እና በጀት ያልተጠናቀቁ ፕሮጀክቶች ክትትል እና ቁጥጥሩ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ሲሉ የቋሚ ኮሚቴው አባላት አስገንዝበዋል፡፡
ቅንጅታዊ አሰራርን በሚመለከት የባለድርሻ አካላትን በማሰባሰብ ከቋሚ ኮሚቴው፣ ከፌደራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት፣ ከገንዘብ ሚኒስቴር እና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በትብብር መስራት እንዳለባቸው ተናግረዋል።
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መስሪያ ቤት ዋና ኦዲተር ክብርት ወ/ሮ መሰረት ዳምጤ የተሰሩ አበረታች ስራዎች እንዳሉ ሆነው የክዋኔ ኦዲት ግኝቱን በአዋጁ መሰረት እንደተመረመሩ ገልፀው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከገንዘብ ሚኒስቴር ጋር በትብብር እንዲሰራ፤ ነባር እና አዲስ ፕሮጀክቶች ተለይተው እንዲቀመጡ መረጃዎች በዳታ ቤዝ መያዝ እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡
የተበላሹ አሰራሮችን ለማሻሻል ሪፎርም እየተተገበረ መሆኑን አንስተው የኦዲት ግኝቱን መሰረት በማድረግ ለመፈፀም ተግዳሮት የሆኑ ህጎችን ማሻሻል እንደሚቻል ጠቁመዋል።
በተጠናቀቁ ፕሮጀክቶች ላይ በጀት ሲመደብ የነበረበትን ምክንያት በሚመለከተው አካል ጥናትና ምርመራ ተደርጎ ተጠያቂነት እንዲሰፍን በማድረግ ሪፖርት እንዲያቀርብላቸው አሳስበዋል።
የአዋጭነት ጥናት ሳይጠና በጀት የተመደበላቸው ፕሮጀክቶችን ከአዋጁ በፊት ነው ወይስ በኋላ የሚለውን በመለየት መረጃ በማደራጀት በሪፖርት እንዲያቀርቡ ሰብሳቢዋ አሳስበዋል፡፡
የፕላንና ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) መንግስት ፕሮጀክቶች ላይ ያሉ ክፍተቶችን ለማረም በርካታ ስራዎች እየሰሩ መሆናቸውን ገልጸው፤ ህግና ሥራዓትን አክብረው በማይሰሩ ተቋማት ላይ ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ የባለድርሻ አካላት ተሳትፎ መኖር እንዳለበት አስረድተዋል፡፡
ከአዋጁ በፊትና በኋላ ያሉ የክዋኔ ኦዲት ክፍተቶችን የፌዴራል ዋና ኦዲተር እና ቋሚ ኮሚቴው እገዛ በማድረግ በአዋጁ ላይ ያሉትን ባለድርሻ አካላት በጋራ በመገምገም ችግሩን ለመፍታት አጋዥ እንደሆናቸው አስተያየት ሰጥተዋል።
(በ የትናየት አሊ)