"የባህር በር ባለቤትነት የትውልድ ጥያቄ ነው"
--- ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ----
(ዜና ፓርላማ) ታህሳስ 21፣ 2018 ዓ.ም፤ 6ኛው የሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት ዛሬ ባካሄደው 6ኛ መደበኛ ስብሰባ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) ከምክር ቤት አባላት ለቀረበላቸው ጥያቄዎች የሰጡትን ምላሽና ማብራሪያ አዳምጧል።
ኢትዮጲያ ያቀረበችው የባህር በር ጥያቄ የመንግሥት ወይም የአንድ ፓርቲ ጥያቄ ብቻ ሳይሆን ትውልድ ተሻጋሪ ግብ ያለው የትውልድ ጥያቄ እንደሆነ ሚንስትሩ ገልጸዋል።
የኢትዮጵያን የባሕር በር ባለቤትነት ለማረጋገጥ ሚንስቴር መስሪያ ቤቱን ጨምሮ የተለያዩ ኢትዮጵያዊያን እና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን ከፍተኛ ስራ እያከናወኑ መሆኑንም ጌዲዮን (ዶ/ር) ባቀረቡት ማብራሪያ ገልጸዋል።
ለዚህም ከመንግስት ምንም አይነት ድጋፍ ሳይደረግላቸው በተለያዩ የሚዲያ አማራጮች እየታገሉ ላሉ ዜጎች ሚንስትሩ ምስጋና አቅርበዋል።
በተለያዩ ሀገራት የሚገኙ የኢትዮጵያ ኤምባሲዎችም የሀገሪቱን የባሕር በር ፍላጎት ለማሳካት እያከናወኑት ያለው ተግባር አበረታች እንደሆነም ገልጸዋል።
በቀጣይም የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስከበር በሚደረገው ዲፕሎማሲያዊ ጥረት ሁሉም ዜጋ የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ሊወጣ እንደሚገባ ሚንስትሩ ጠቁመዋል።
(በአበባው ዮሴፍ)




ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
በፌስቡክ http://www.facebook.com/hoprparliament
በዩቲዩብ
https://www.youtube.com/@FDREHOPR
በቴሌግራም
https://t.me/ParlamaNews
በትዊተር
http://twitter.com/fdrehopr
በዌብሳይት
www.hopr.gov.et ይከታተሉ።